ቀጥታ፡

ኮርፖሬሽኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 35 ባለሀብቶችን ወደ ስራ አስገብቷል

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ የኦሮሚያ ክልል ኢንዱስትሪ ልማት ፓርኮች ኮርፖሬሽን በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት 35 ባለሀብቶችን ተቀብሎ ወደ ስራ ማስገባት መቻሉን ገለጸ። 

ኮርፖሬሽኑ በተለይ የገቢ ምርቶችን በሚተኩ የልማት ዘርፎች ላይ ትኩረት አድርጎ በመስራቱም ውጤታማ ጅምር መኖሩን አረጋግጧል።

በኮርፖሬሽኑ የልማት ዘርፍ ምክትል ስራ አስፈጻሚ አቶ ሰለሞን ቱፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኮርፖሬሽኑ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን የማልማት ፣ የማስተዳደርና ገቢ የማመንጨት ተልዕኮውን በስኬት እየተወጣ ይገኛል።

በበጀት ዓመቱም ባለሀብቶች በቡልቡላ የተቀናጀ ኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ በመካከለኛ ኢንዱስትሪ ማዕከላት፣ ጥቃቅን ኢንዱስትሪ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ገቢን ለማመንጨትና ተኪ ምርቶችን ለማምረት  ወደ ስራ መግባታቸውንም ነው የገለጹት።


 

ባለሀብቶቹ በዋናነት በምግብ ዘይት፣ በጥራጥሬና ፍራፍሬ ልማት እንዲሁም በተለያዩ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፎች ላይ መሰማራታቸውን ተናግረዋል።

ባለሀብቶቹ ስራ የጀመሩት መሰረተ ልማት በተሟላላቸው ስፍራዎች መሆኑን የገለጹት አቶ ሰለሞን፣ በዋናነትም የቡልቡላ የተቀናጀ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ እና በስሩ የሚገኙ 6 መካከለኛ ኢንዱስትሪ ማዕከላት መሆናቸውን ጠቁመዋል።

በበጀት ዓመቱም 35 ባለሀብቶችን ወደ ማምረት ስራ ማስገባት በመቻሉ በአጠቃላይ የአልሚ ባለሀብቶች ቁጥር 81 ደርሷል ብለዋል።

በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት 3 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሊትር የምግብ ዘይት በኮርፖሬሽኑ ስር በሚገኙ ፓርኮች ተመርቶ ለገበያ የቀረበ ሲሆን፣ ከዚህም 1 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ገቢ ተገኝቷል ብለዋል።


 

ወደ ስራ በገቡት አምራች ኢንዱስትሪዎች  3 ሺህ 225 ዜጎች የስራ ዕድል ማግኘታቸውንም አስታውቀዋል።

በነቀምቴ የተቀናጀ ኢንዱስትሪ ፓርክ ከለማው 60 ሄክታር መሬት ውስጥ 10 ሄክታሩ ለባለሀብቶች የተላለፈ ሲሆን ከተገነቡት ሶስት ሼዶች መካከል ሁለቱ ለባለሀብቶች እንዲተላለፉ መደረጉንም ገልፀዋል።

ኮርፖሬሽኑ በቀጣይም የለሙ መሬቶችን በማቅረብና አምራቾች ምርቶቻቸውን በስፋት ለገበያ እንዲያቀርቡ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ምክትል ስራ አስፈጻሚው አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም