ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ይካሄዳል፡፡

የጎዳና ላይ ሩጫውን በተመለከተ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል።

የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ አስተባባሪ አብዱልፈታህ የሱፍ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ይካሄዳል።

የሩጫ ውድድሩ ገቢ ምርትን በመተካት የተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች የስፖርት አልባሳትን ማስተዋወቅ እና የማምረት አቅማቸውን ማሳየትን አላማ ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

ዜጎች የሀገር ውስጥ ምርትን የመጠቀም ባህል እንዲያሳድጉ ግንዛቤ የሚፈጠርበት መሆኑንም አመላክተዋል።

ውድድሩ አዲስ አበባ ከተማ ያላትን የቱሪዝም ሀብት ለማስተዋወቅ ተጨማሪ እድል እንደሚፈጥርም እንዲሁ።

በውድድሩ ከ15 ሺህ በላይ ተሳታፊዎች እንደሚገኙ እና ከእነዚህ ውስጥ 500 የሚሆኑት አትሌቶች መሆናቸውን ተናግረዋል።

በዚህ ውድድር በሴቶችና በወንዶች 1ኛ ለሚወጡ 550 ሺህ ብር፣ 2ኛ ደረጃን ለሚይዙ 300 ሺህ ብር እንዲሁም በ3ኛነት ለሚያጠናቅቁ ደግሞ 200 ሺህ ብር እንደሚበረከት ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የተሳትፎና ውድድር ዳይሬክቶሬት ተወካይ ጊዜ አድነው በበኩላቸው፤ የጎዳና ላይ ሩጫው ለአትሌቶች አዲስ የውድድር እድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም