ቀጥታ፡

በክልሉ ከ2 ሺህ 800 በላይ ትራክተሮችን በማሰማራት ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል

ባህርዳር ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በቀጣዩ የመኸር ወቅት ከ2 ሺህ 800 በላይ ትራክተሮችን በማሰማራትና በሜካናይዜሽን እርሻ ተጨማሪ ምርት በማምረት ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት መደረጉ ተገለፀ።

በክልሉ ግብርና ቢሮ የግብርና ግብዓትና የገጠር ፋይናንስ አቅርቦት ዳይሬክተር ወይዘሮ ሙሽራ ሲሳይ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ የክልሉ አርሶ አደር የምግብ ዋስትናውን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት እንዲያመርት እየተሰራ ነው።


 

በኩታ ገጠም በማልማት፣ የሜካናይዜሽን አሰራርን በመከተል፣ ግብዓትንና ሌሎች ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ በመጠቀም የምርት ጭማሪውን ለማሳካት ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

‎‎በዚህም በአርሶ አደሩና በባለሃብቱ እጅ የሚገኙ ከ2 ሺህ 800 በላይ የእርሻ ትራክተሮችን በማሰማራት 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በሜካናይዜሽን ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አስረድተዋል።

ከዚህ ውስጥም 683 የእርሻ ትራክተሮችና 12 ኮምባይነሮች በያዝነው በጀት ዓመት የተሰራጩ በመሆኑ ምን ያህል ለዘርፉ ትኩረት እንደተሰጠ ማሳያ ነው ብለዋል።

‎በተጨማሪም ‎የምርት ብክነትን ለመቀነስም ከወዲሁ ከአንድ ሺህ በላይ አነስተኛ የሰብል መውቂያና የበቆሎ መፈልፈያ ማሽኖችን  ለአርሶ አደሮች ተደራሽ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል።

አሁን እየጣለ የሚገኘው ዝናብም ለእርሻ ስራ አመቺ በመሆኑ አርሶ አደሩ በቴክኖሎጂ ታግዞ የእርሻ ስራውን ከወዲሁ አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አሳስበዋል።

በምዕራብ ጎጃም ዞን የወንበርማ ወረዳ አርሶ አደር ባዩ ተጃረ ፤ በበቆሎና ስንዴ ሰብል የሚያለሙትን ሁለት ሄክታር መሬት በትራክተር ለማረስ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።


 

ዘንድሮ ቀድሞ መጣል የጀመረው ዝናብ የእርሻ ስራ ለማከናወን ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ጠቁመው መሬቱን ቀድሞ በማለስለስ በወቅቱ ለመዝራት መዘጋጀታቸውን አስረድተዋል።  

በትራክተር ማረስ የሚያስገኘውን ጥቅም በመገንዘብ ከሁለት ሄክታር በላይ ማሳቸውን በሜካናይዜሽን ለማልማት መዘጋጀታቸውን የገለጹት ደግሞ የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ተመስገን ታደለ ናቸው።

ይህም የአርሶ አደሩን ጊዜና ጉልበት ከመቆጠብ በተጨማሪ ለሰብል ምርታማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑን አስረድተዋል። 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም