ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና ዲጂታል ቴክኖሎጂዎች ዘርፍ ያላትን ልምድ ለአህጉሩ ለማካፈል ቁርጠኝነቷን ዳግም ታረጋግጣለች 

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና ዲጂታል ቴክኖሎጂዎች ዘርፍ ያላትን ልምድ ለአህጉሩ ለማካፈል ቁርጠኝነቷን ዳግም ታረጋግጣለች ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።

በፍጥነት ከሚለዋወጠው የቴክኖሎጂው ዓለም ጋር ውጤታማ በሆነ መልኩ መራመድ የሚያስችሉ ጠንካራ አጋርነቶችን ለመመሥረት ያላትን ቁርጠኝነትም እንዲሁ ዳግም ታረጋግጣለች ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ሕብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) በመሆን አዲስ ኃላፊነት ተሰጥቷቸዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ዛሬ ጠዋት የአፍሪካ በሽታ መቆጣጠሪያ እና መከላከያ ማዕከል (Africa CDC) ዋና ዳይሬክተር ከሆኑት ከዶክተር ዣን ካሴያ ጋር ውጤታማ ውይይት አድርገናል ብለዋል።

በውይይታችንም በተለያዩ ቅድሚያ የሚሰጣቸው ጉዳዮች ላይ የመከርን ሲሆን፤ በተለይም በአፍሪካ ሕብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) በመሆን የተሰጠኝን አዲስ ኃላፊነት በሚመለከት በስፋት ተነጋግረናል ነው ያሉት።

በዚህም ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን ልምድ ለአህጉሩ ለማካፈል እንዲሁም በፍጥነት ከሚለዋወጠው የቴክኖሎጂው ዓለም ጋር ውጤታማ በሆነ መልኩ መራመድ የሚያስችሉ ጠንካራ አጋርነቶችን ለመመሥረት ያላትን ቁርጠኝነት ዳግም ታረጋግጣለች ሲሉ ገልጸዋል።

የፈጠራ ሥራዎች ለአፍሪካ ዕድገት ምንጊዜም ወሳኝ መሰረት መሆናቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት ጠቁመዋል።

በጤናው ዘርፍ የሚገጥመንን ተለዋዋጭ ተግዳሮቶች ለመወጣት የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን ዐቅም መጠቀም የጤና ሥርዓታችንን ለማጠናከር፣ ተደራሽነትን ለማስፋፋት እና ለሕዝባችን የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ወሳኝ ነው ብለዋል።

በመሆኑም ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን ልምድ ለአህጉሩ ለማካፈል እንዲሁም በፍጥነት ከሚለዋወጠው የቴክኖሎጂው ዓለም ጋር ውጤታማ በሆነ መልኩ መራመድ የሚያስችሉ ጠንካራ አጋርነቶችን ለመመሥረት ቁርጠኛ መሆኗንም ገልጸዋል።

ይህንን ርዕይ ወደ ተጨባጭና አካታች ውጤት ለመለወጥ ከአፍሪካ ሲዲሲ (Africa CDC) እና በመላው አህጉሪቱ ከሚገኙ አጋሮች ጋር በቅርበት ለመሥራት ዝግጁ ነኝ ሲሉም አረጋግጠዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም