ተሻሽሎ የፀደቀው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ የሀገራችንን የአየር ትራንስፖርት ዕድገት አንድ ደረጃ ከፍ ያደርገዋል - ኢዜአ አማርኛ
ተሻሽሎ የፀደቀው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ የሀገራችንን የአየር ትራንስፖርት ዕድገት አንድ ደረጃ ከፍ ያደርገዋል
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018(ኢዜአ)፦ ተሻሽሎ የፀደቀው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ የሀገራችንን የአየር ትራንስፖርት ዕድገት አንድ ደረጃ ከፍ እንደሚያደርገው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ገለጸ።
6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው 15ኛ መደበኛ ስብሰባ የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅን ለማሻሻል የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ 1412/18 መርምሮ አጽድቋል፡፡
የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ በላከው መረጃ እንዳመለከተው፤ ከ21 ዓመታት በኋላ ተሻሽሎ የፀደቀው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ ተቋሙ የአቪዬሽን ደኅንነት ሥራዎችን በበላይነት ለመምራት እና ለማስተባበር የተሰጠውን ሀገራዊ ተልዕኮ ከስያሜው አንስቶ በግልፅ ያካተተ ሲሆን፤ የሀገራችንን የአየር ትራንስፖርት ዕድገት አንድ ደረጃ ከፍ ለማድረግ ያግዛል፡፡
የአቪዬሽን ደኅንነትን ለማጠናከር ትኩረት ከሚሰጣቸው ጉዳዮች ውስጥ የመጀመሪያው የሕግ ማዕቀፍ መሆኑንም አገልግሎቱ በመረጃው አመላክቷል።
በዚህ ረገድ ነባሩ አዋጅ ኢንዱስትሪውን በሚፈለገው ደረጃ ለማሳደግ ተግዳሮት ሆኖ ከመቆየቱም በላይ የዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት (ICAO) ተቀጽላ 17 ስታንዳርዶችን ሳያካትት መቆየቱንም ጠቁሟል፡፡
ተሻሽሎ የፀደቀው አዋጅ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የተሰጠውን የአቪዬሽን ደኅንነትን የማረጋገጥ ሀገራዊ ተልዕኮ በላቀ ብቃት ከመወጣት አንፃር የጥራትና የቁጥጥር ስራዎች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን ጠብቀው እንዲከናወኑ የሚያስችሉ ሕጎችን መያዙም ተመላክቷል፡፡
አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ በአቪዬሽን ደኅንነት ረገድ ላስቀመጠው ራዕይ እና ስትራቴጂክ ግብ ስኬት መሰረት የሚጥል መሆኑም ጠቅሷል፡፡
ከቴክኖሎጂ አንፃር ኢንዱስትሪውን ለማዘመን አስፈላጊ የሆኑ ባለድርሻ አካላትን በኮሚቴነት መጨመሩ፤ የዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት ስታንዳርዶችን በአዲስ መልክ ማካተቱ፤ የአየር መንገዱን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ እገዛ የሚያደርግ መሆኑና ከኢንዱስትሪው ፈጣን እድገት ጎን ለጎን ለመጓዝ አቅም መፍጠር የሚያስችል የሕግ ድጋፍ መስጠቱ በፋይዳነት የሚጠቀሱ መሆናቸውንም በመረጃው ተገልጿል፡፡
የተሻሻለው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ ቁጥር 1412/18 በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሚያዝያ 13 ቀን 2018 ዓ.ም በአብላጫ ድምጽ መጽደቁንም አገልግሎቱ በመረጃው አመልክቷል፡፡