ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከማዕድን ዘርፍ ወጪ ንግድ አራት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ ተገኝቷል - ኢዜአ አማርኛ
ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከማዕድን ዘርፍ ወጪ ንግድ አራት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ ተገኝቷል
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከማዕድን ዘርፍ ኤክስፖርት አራት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ መገኘቱን የማዕድን ሚኒስትር ኢንጅነር ሀብታሙ ተገኝ ገለጹ፡፡
የ2018 በጀት ዓመት ሦስተኛው የመቶ ቀናት እና የዘጠኝ ወራት ስራ አፈጻጸም ሪፖርት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተገምግሟል።
የማዕድን ሚኒስትሩ ኢንጅነር ሀብታሙ ተገኝ በሰጡት ማብራሪያ፣ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከማዕድን ወጪ ንግድ ወደ አራት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ መገኘቱን ይፋ አድርገዋል።
እንደ ሚኒስትሩ ማብራሪያ፣ በዘርፉ የታየው ውጤት ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ87 በመቶ እድገት አሳይቷል።
ይህ የአራት ቢሊዮን ዶላር ገቢ ከሦስት ዓመታት በፊት የሀገሪቱ አጠቃላይ ዓመታዊ የኤክስፖርት ገቢ የነበረውን ያህል መሆኑ፣ ዘርፉ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያመጣውን ግዙፍ ለውጥ ያመላክታል ብለዋል።
ለዘርፉ ስኬት ዋነኛው ምክንያት የሀገሪቱ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያ መሆኑን ጠቁመዋል።
በተለይም ባለሀብቶች ያገኙትን ትርፍ በውጭ ምንዛሬ ወደ ውጭ ማውጣት መቻላቸው፤ የኢንቨስትመንት ስጋቶች መቀነሳቸው እና መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ የማበረታቻ ሥርዓት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቁ ግዙፍ ኩባንያዎች ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ አድርጓል ነው ያሉት።
ከወርቅ ባለፈ ሌሎች ማዕድናትም ትኩረት እንደተሰጣቸው አንስተዋል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ከፍተኛ የወርቅ ሀብት ካላቸው ሀገራት ተርታ እየተሰለፈች ሲሆን፥ ከወርቅ በተጨማሪ ሌሎች ማዕድናት ላይ ትኩረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
እስካሁን በፍለጋ ደረጃ የነበሩ እንደ ጋዝ፣ ፖታሽ፣ ሊቲየም እና ኒኬል ያሉ ማዕድናት ወደ ምርት እንዲገቡ እየተደረገ መሆኑን ነው ያነሱት።
እነዚህ ማዕድናት በቀጣይ የዘርፉን የኤክስፖርት ገቢ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሳድጉትም አንስተዋል።
ከማዕድን ወጪ ንግድ ባሻገር እንደ ብረት፣ ሲሚንቶ እና ድንጋይ ከሰል ያሉ ማዕድናት የሀገር ውስጥ ፍላጎትን በማሟላት የውጭ ምንዛሬን ለማዳን ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ ነው ያሉት።
ከሀገር ውስጥ ፍላጎት የሚተርፈው ምርት ደግሞ ወደ ውጭ ገበያ እንደሚላክ አስረድተዋል።
አዲስ የተረቀቀው የማዕድን ፖሊሲ ሲጸድቅ እና አሁን የተጀመረው የሪፎርም ስራ ተጠናክሮ ሲቀጥል፣ ዘርፉ ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ይበልጥ እንደሚያድግ አብራርተዋል።