አሜሪካ ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ያላትን ድጋፍ አረጋገጠች - ኢዜአ አማርኛ
አሜሪካ ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ያላትን ድጋፍ አረጋገጠች
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፦ አሜሪካ ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ጠንካራ ድጋፍ መስጠቷን የገንዘብ ሚኒስቴር አስታወቀ።
ኢትዮጵያ ለአውሮፕላን ማረፊያው ፕሮጀክት የሚውል የገንዘብ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በዋሽንግተን ዲሲ አድርጋለች።
በመድረኩ ላይ ኢትዮጵያ ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ከአሜሪካ መንግሥት ተቋማት፣ ከታዋቂ የፋይናንስ ተቋማት እና ከዘርፉ ግዙፍ ኩባንያዎች ጠንካራ ድጋፍ አግኝታለች።
ድጋፉ በአፍሪካ ግዙፍ ከሆኑ የአቪዬሽን መሠረተ ልማቶች አንዱ የሆነውን ይህን ፕሮጀክት እውን ለማድረግ እንደሚያስችል ተመላክቷል።
ከፍተኛ የአሜሪካ መንግሥት ባለሥልጣናት ኢትዮጵያ ግልጽነት የሰፈነበትና በግል ዘርፉ የሚመራ ኢኮኖሚ ለመገንባት ለጀመረችው የሪፎርም ጉዞ ያላቸውን ጽኑ ድጋፍና እምነት ገልጸዋል።
ባለሥልጣናቱ የሀገሪቱን የማክሮ ኢኮኖሚ አፈጻጸምና ተስፋ ሰጪ የዕድገት ጉዞ አድንቀው፤ ይህም ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት አስተማማኝ ዋስትና እንደሚሆን አመልክተዋል።
የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የአፍሪካን አህጉራዊ ትስስር የሚቀይር፣ የንግድ ፍሰትን የሚያሳልጥና ኢትዮጵያን ቀዳሚ ዓለም አቀፍ የአቪዬሽንና የሎጂስቲክስ ማዕከል የሚያደርግ ከፍተኛ ፋይዳ ያለው ኢንቨስትመንት መሆኑ ተጠቁሟል።
ፕሮጀክቱ አህጉሪቱን ከዓለም አቀፍ የንግድና የኢኮኖሚ መረቦች ጋር በላቀ ደረጃ እንደሚያስተሳስርና የኢኮኖሚ ትብብሩን እንደሚያጠናክር ይጠበቃል።
ይህ ግዙፉ ፕሮጀክት በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ያለውን የንግድ ትብብር ይበልጥ እንደሚያጠናክርና ወደ አዲስ ምዕራፍ እንደሚያሸጋግርም ተመልክቷል።
የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሽግግር ከመደገፉም በላይ፣ ለአሜሪካ ኩባንያዎችና የፋይናንስ ተቋማት ሰፊ የንግድ ዕድሎችን የሚፈጥር በመሆኑ የሁለቱን ሀገራት የጋራ ጥቅም የሚያስጠብቅ መሆኑ ተገልጿል።
የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ የቢሾፍቱ አየር ማረፊያ ለአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ትስስር ካለው ጠቀሜታ በተጨማሪ፣ ለንግድና ለኢንቨስትመንት ዕድገት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት አመልክተዋል።
ሚኒስትሩ አክለውም አውሮፕላን ማረፊያው ዓለም አቀፋዊ ፋይዳ ያለውና ቅድሚያ የሚሰጠው ሀገራዊ ፕሮጀክት መሆኑን ጠቅሰው፤ በዋሽንግተን የታየው ድጋፍ በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ መፃኢ ዕድል ላይ ያለውን እምነት የሚያንፀባርቅ መሆኑን አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ከአሜሪካ አጋሮች ጋር ያለው ትብብር ለአየር መንገዱ የስኬት መሠረት መሆኑን ጠቅሰው፣ ፕሮጀክቱ አዲስ አበባን ግንባር ቀደም የአቪዬሽን ማዕከል ለማድረግ እንደሚያስችል ገልጸዋል።
የፕሮጀክቱ ዋና አስተባባሪ የሆነው የአፍሪካ ልማት ባንክ በበኩሉ፣ ፕሮጀክቱ በኢኮኖሚያዊ አዋጭነቱና በቀጣናዊ ውህደት ላይ ባለው ፋይዳ ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው መሆኑን አብራርቷል።
የባንኩ ምክትል ፕሬዝዳንት ሀሳቱን ሴሌ አውሮፕላን ማረፊያው በአፍሪካ ዘላቂ እድገትን ለማምጣት ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል።
በዋሽንግተኑ ምክክር በፋይናንስ መዋቅርና በተግባር አፈጻጸም የታዩ ውጤቶች የተዳሰሱ ሲሆን ፕሮጀክቱን ለማፋጠን የሚያስችሉ ቁልፍ ግብዓቶች ተገኝተዋል።
ይህ እርምጃ አህጉራዊ ፋይዳ ያለውንና ግዙፉን የአቪዬሽን ፕሮጀክት ውጤታማ ለማድረግ የሚከናወነውን እንቅስቃሴ ለማፋጠን የላቀ ሚና ይጫወታል።
በኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚመራው ይህ ፕሮጀክት፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመጣው የመንገደኞችና የጭነት አገልግሎት ፍላጎት ላይ የተመሰረተ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አስታውቋል።