ቀጥታ፡

የአፍሪካ የዲጂታል ድምጾች ለጠንካራ ዓለም አቀፍ ትርክት ግንባታ ወሳኝ ናቸው

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ የዲጂታል ድምጾች ለጠንካራ ዓለም አቀፍ ትርክት ግንባታ ወሳኝ መሆናቸውን የ ፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍጹምሸት ሽመልስ ገለጹ።

አዲስ አበባ እ.አ.አ 2026 በመጪው ግንቦት 7 እና 8 ቀን የአፍሪካ የማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ጉባኤን (ASMIS-2026) በዓድዋ ድል መታሰቢያ ለማስተናገድ ዝግጅት እያደረገች ይገኛል።


 

አህጉራዊ ጉባኤውን በስኬት ለማስተናገድም ፐልስ ኦፍ አፍሪካ (Pulse of Africa-POA) እና ኤጂኤ ቴክ (AGA-Tech) የባለድርሻና ተባባሪ አካላት የምክክር መድረክ አካሂደዋል።

የመድረኩ ዓላማም ጉባኤውን በስኬት ማስተናገድ በሚቻልባቸው የዝግጅት ሂደትና የትብብር ድጋፎች ላይ ትኩረት አድርጓል።

በዚሁ ጊዜ የአፍሪካ የማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ጉባኤ በተፅዕኖ ፈጣሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ በአፍሪካ ዳያስፖራዎችና የግሉ ዘርፍ ተዋናዮች የረጅም ጊዜ ትብብር የሚፈጠርበት መሆኑ ተገልጿል።

የፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍጹምሸት ሽመልስ በዚሁ ወቅት፤ የአፍሪካ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን የአህጉሪቱን ዓለም አቀፍ አመለካከት የሚቀይር ታሪካዊ ዕድል ነው ብለዋል።


 

በማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች በአፍሪካ ዙሪያ የሚፈጠሩ፣ የሚቀረጹና የሚሰራጩ ትርክቶች ዓለም ለአህጉሪቱ የሚሰጠውን የተሳሳተ ግምት ለመቀየር ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ገልጸዋል።

የማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ጉባኤም የአፍሪካን ትክክለኛ ታሪክ፣ ስኬትና ምኞት የበለጠ ለማጉላት የዲጂታል ይዘት ፈጣሪዎችን አቅም ማጎልበት እንደሚያስችል ተናግረዋል።

ኤጂኤ ቴክ (AGA-Tech) ኢንተርፕራይዝ ሥራ አስኪያጅ ገመዳ ኦላና በበኩላቸው፤ በርካታ የአፍሪካ ማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች በጉባኤው ለመሳተፍ ከፍተኛ ፍላጎት እያሳዩ መሆኑን ገልጸዋል።


 

በጉባኤው የአፍሪካን ትርክት የሚያጎላ ጠንካራና ተቀባይነት ያለው የይዘት ፈጠራ ሥነ-ምኅዳር ግንባታ ላይ ትኩረት እንደሚደረግ ተናግረዋል።

መድረኩ የባለድርሻ አካላትን ትብብር በማጠናከር የአህጉሪቱን የይዘት ጥራትና ፈጠራ በማሻሻል ተወዳዳሪ የዲጂታል ኢኮኖሚን ለመደገፍ ያለመ ነው ብለዋል።

በተሳታፊዎች መካከልም በአጋርነት፣ ቅንጅት፣ ተግባቦት፣ ስትራቴጂክ አመራርና በሃብት ማሰባሰብ ጉዳዮች ላይ ጥልቅ ምክክር እንደሚደረግ አስረድተዋል።

በአጠቃላይ ጉባኤው የዲጂታል ድምጾችን በማስተሳሰር የአህጉሪቱን ታሪክ የመንገር አቅም የሚያጎለብትና ዓለምአቀፍ ተፅዕኖ ፈጣሪነትንና ንቁ ተዋናይነትን የሚያጠናክር መሆኑን አብራርተዋል።

በውይይቱ ጉባኤው ትርጉም ያለውና ዘላቂ ተጽዕኖ እንዲያሳድር ትብብርና የጋራ ጥረት አስፈላጊ መሆኑንና ባለድርሻ አካላት ለጉባኤው ስኬት ገንቢ ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም