ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ ለባለብዙ ወገን ዓለም አቀፍ የንግድ ስርዓት ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ ናት

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ በሁሉን አቀፍ ማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለሃገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች ለንግድና ኢንቨስትመንት ምቹ ከመሆን ባለፈ ለባለብዙ ወገን ዓለም አቀፍ የንግድ ስርዓት ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆኗን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ።


 

የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት 7ኛው የስራ ቡድን ስብሰባ በስዊዘርላንጅ ጄኔቫ በይፋ መካሄድ ጀምሯል።

ሚኒስትሩ በስብሰባው መክፈቻ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት የኢትዮጵያን የአባልነት ጉዞ በማፋጠን ረገድ የስራ ቡድን ስብሰባ ሊቀመንበር፣ ሴክሬታሪያትና አባላት ላደረጉት ያላሰለሰ ድጋፍና ንቁ ተሳትፎ አመስግነዋል።

ባለፈው መስከረም ከተካሄደው 6ኛው የስራ ቡድን ስብሰባ ወዲህ ኢትዮጵያ በባለብዙ ወገንና በሁለትዮሽ ድርድሮች ከፍተኛ እመርታ አሳይታለች ብለዋል።

ለ226 የአባል ሃገራት ጥያቄዎች ጥልቅ ምላሾችን የመስጠት፣ የስራ ቡድን ረቂቅ ሪፖርትን የማዳበርና 32 የግዴታ አንቀጾችን የማጠናቀቅ ስራ መከናወኑንም በመድረኩ ላይ አብራርተዋል።


 

ከ9 አባላት ጋር የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ድርድሮችን አጠናቀናል ሲሉም ሚኒስትሩ ገልጸዋል።

በተጨማሪም ኢትዮጵያ ከአባላት የተነሱ ወሳኝ ቀሪ ጉዳዮችን በዳበረ ይዘትና ገንቢ አካሄድ ለማከናወን ቁርጠኛ መሆኗን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ በሁሉን አቀፍ ማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለሃገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች ለንግድና ኢንቨስትመንት ምቹ ከመሆን ባለፈ ለባለብዙ ወገን ዓለም አቀፍ የንግድ ስርዓት ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆኗንም አረጋግጠዋል።

7ኛው የስራ ቡድን ስብሰባ ዛሬ ቀኑን ሙሉና ነገም ቀጥሎ የሚካሄድ መሆኑን ኢዜአ ከስፍራው ያገኘው መረጃ ያመለክታል።

#Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም