ቀጥታ፡

የግብርና ትራንስፎርሜሽንን ከግብ ለማድረስ የኀብረት ሥራ ማህበራትና ዩኒየኖች ሚና የላቀ ነው

አዳማ፤ ሚያዚያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የተጀመረውን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ከግብ ለማድረስ የኀብረት ሥራ ማህበራት ዩኒየኖችና ባለሙያዎች ሚና የላቀ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አመለከተ።

የኢትዮጵያ ህብረት ስራ ኮሚሽን "ወደ ቀበሌ መድረስ" በሚል መሪ ሃሳብ ያዘጋጀው 2ኛው ሀገር አቀፍ የህብረት ስራ ሪፎርም የንቅናቄ መድረክ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እየተካሔደ ነው።

የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤልያስ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ ሀገሪቱ ግብርናን ዋነኛ የኢኮኖሚ ማእከል በማድረግ ወደ ኢንዱስትሪ ለመሸጋገር እየተጋች ትገኛለች።

ለዚህም ባለፉት የለውጥ ዓመታት በመንግሥት የግብርና ትራንስፎርሜሽን ተነድፎ በተደረገው ርብርብ ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል።

ከተገኘው ውጤት ውስጥ አንድም መሬት ጦም እንዳያድር በሚል መርህ በየደረጃው በተደረገው ንቅናቄ በዓመት የሚለማውን መሬት ከ14 ሚሊዮን ወደ 22 ሚሊዮን ማሳደግ መቻሉን አውሰተዋል።

ከለውጡ በፊት 500 ሚሊዮን ኩንታል ብቻ የነበረው ዓመታዊ የሰብል ምርት ከሶስት እጥፍ በላይ ማሳደግ መቻሉንም አስረድተዋል።

በዚህም የተጀመረውን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ትግበራ ከግብ ለማድረስ የኀብረት ሥራ ማህበራትና ዩኒየኖች ሚና የላቀ መሆኑንም አመልክተዋል።

ለዚሁ ስኬትም የኀብረት ስራ ማህበራትና ዩኒየኖች ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘር እና ሌሎች ግብዓቶችን በበቂ ሁኔታ በማቅረብ እያከናወኑት ያለውን ተግባር ሊያጠናክሩ ይገባል ብለዋል።

በግብርና ሚኒስቴር የግብዓትና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤ ግብርናና ኀብረት ስራ ማህበራት ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ ያላቸው አበርክቶ ሰፊ መሆኑን ጠቁመዋል።

በተለይ ኀብረት ስራ ማህበራት በውጭ ግብይት ተሳትፎ፣ በብድርና ቁጠባ ረገድ ያላቸው አስተዋጽኦ እያደገ መምጣቱን ገልፀው፤ በግብርና ምርት ግብይት ረገድ የመሪነት ሚናቸውን በአግባቡ ሊወጡ እንደሚገባም አመልክተዋል።

ኮሚሽኑ ባዘጋጀውና ለተከታታይ ስምንት ቀናት በሚቆየው ሀገር አቀፍ የኀብረት ስራ የልማት አመቻች ባለሙያዎች ስልጠና ላይ ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ 4 ሺህ የቀበሌ አደራጅ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም