በኢንዱስትሪ እንቅስቃሴ ውስጥ የሴቶች ንቁ ተሳትፎ ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ግንባታ የጎላ ሚና አለው - ኢዜአ አማርኛ
በኢንዱስትሪ እንቅስቃሴ ውስጥ የሴቶች ንቁ ተሳትፎ ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ግንባታ የጎላ ሚና አለው
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፡- ሴቶች በተለያየ የኢንዱስትሪ እንቅስቃሴ ውስጥ በመሰማራት ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ግንባታ ሚናቸው የጎላ መሆኑን የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስገነዘበ።
ዓለም አቀፉ የኢንዱስትሪ ሴቶች ቀን በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ “ሴቶች የወደፊት ኢንዱስትሪን በመቅረጽ ላይ” በሚል መሪ ሐሳብ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል።
የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ሴቶች በተለያየ የኢንዱስትሪ እንቅስቃሴ ውስጥ በመሰማራት ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ግንባታ የጎላ ሚና አላቸው ብለዋል።
ሴቶችን ከማብቃት ጎን ለጎን በሙሉ ዐቅማቸውና በእኩልነት በዘርፉ ትርጉም ያለው ተሳትፎ እንዲያደርጉ፤ በአምራችነት፣ በአመራርነትም ሆነ በፈጠራ ረገድ በዓለም አቀፍ ደረጃ ብቁና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ሁላችንም በትብብር መሥራት ይጠበቅብናል ነው ያሉት።
የበዓሉ መከበር በኢንዱስትሪ ዘርፍ የተሰማሩ ሴቶች የበለጠ ትኩረት እንዲያገኙ፣ የሚያጋጥሟቸው ችግሮች እንዲፈቱ እና በዘርፉ ራሳቸውንም ሆነ ሀገራቸውን እንዲጠቅሙ አስተዋፅዖ እንዳለው ጠቁመዋል።
በተጨማሪም ለሥርዓተ ጾታ አካታችነትና ለዘላቂ የኢንዱስትሪ ልማት ያለንን ቁርጠኛነት የሚያጠናክር ነው ያሉት ሚኒስትሯ፤ የተባበሩት መንግሥታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት /UNIDO/ በዓሉ በኢትዮጵያ እንዲከበር ላበረከተው ሚና አመሥግነዋል።
የዩኒዶ ተወካይና የሰብ ሪጅናል ጀነራል ዳይሬክተር ስቴፈን ካርግቦ (ዶ/ር) በበኩላቸው ተቋማቸው ሴቶችን አካታች ያደረገና ዘላቂ የኢንዱስትሪ ልማት እውን ለማድረግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እንደሚሠራ ገልጸው፤ ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል።