ቀጥታ፡

በኦዲት ዘርፍ በተከናወኑ የሪፎርም ተግባራት ተጨባጭ ለውጦች እየተመዘገቡ ነው -ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ

ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኦዲት ዘርፍ በተከናወኑ የሪፎርም ተግባራት ተጨባጭ ለውጦች እየተመዘገቡ መሆናቸውን የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ ገለጹ።

24ኛው የፌዴራል፣ የክልል እና የከተማ አስተዳደር ዋና ኦዲተሮች ዓመታዊ የምክክር ጉባኤ በጅግጅጋ ተጀመረ። 

የፌዴራል ዋና ኦዲተር ወይዘሮ መሰረት ዳምጤ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ በኦዲት ዘርፍ በተከናወኑ የሪፎርም ተግባራት ተጨባጭ ለውጦች እየተመዘገቡ ነው።

በዘርፉ በተከናወኑ የሪፎርም ስራዎች መሰረት ከአለም አቀፍ፣ አህጉር አቀፍና ቀጣናዊ የኦዲት ተቋማት ጋር የተፈጠሩ ግንኙነቶች ፍሬያማ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል፡፡ 

በፌዴራልና በክልል ደረጃ በሚገኙ አንዳንድ ተቋማት የሚስተዋሉ ብልሹ አሠራሮችን በመቀነስ ረገድ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤት የታየባቸው መሆኑን ጠቁመው፤ ሂደቱን ስኬታማ ለማድረግም ተቋማት ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል።

የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ ሙሀመድ በበኩላቸው ባለፉት ስምንት ዓመታት በክልሉ በርካታ የሪፎርም ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። 

ከነዚህም ውስጥ በፋይናንስ አስተዳደር ዘርፍ የተከናወነው ሪፎርም ከፍተኛ ውጤት እንደተመዘገበበት ገልጸው፤ በዘርፉ የተጠናከረ የክትትልና የቁጥጥር ስራ መሰራቱንም አስረድተዋል፡፡ 

በክልሉ ተግባራዊ በተደረገው የፋይናንስ አስተዳደር አዋጅ መሰረት የህዝብና የመንግስት ሀብት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የሶማሌ ክልል ዋና ኦዲተር አቶ ሙሀመድ ዩሱፍ ናቸው፡፡ 

ጉባኤው ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ ሶስት ቀናት እንደሚካሄድ ተናግረው በአገሪቱ የፋይናንስ ሥርዓት ላይ በተጀመረው የሪፎርም ሥራዎችና የኦዲት ተግባራት ዙሪያ ውይይት ይደረጋል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም