ቀጥታ፡

ማህበራቱ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተመላከተ

ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ህብረት ስራ ማህበራት የኢኮኖሚ ሉአላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት አሻራቸውን ማኖር እንደሚገባቸው በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ።

የኢትዮጵያ ህብረት ሥራ ኮሚሽን “ወደ ቀበሌ መድረስ” በሚል መሪ ሃሳብ 2ኛውን ሀገር አቀፍ የህብረት ሥራ ሪፎርም የንቅናቄ መድረክ በተለያዩ ከተሞች በማካሄድ ላይ ይገኛል።

በንቅናቄው መድረክ ላይ የተገኙት ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፤ መንግስት ባለፉት ስምንት ዓመታት የዜጎችን ብልጽግና ለማረጋገጥ የሚያስችል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ማድረጉን ተናግረዋል።

ማሻሻያው ዜጎች በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ቀጥተኛ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከማድረግ ባለፈ በቤተሰብ ደረጃ ብልጽግናን ለማምጣት በተከናወኑ ተግባራት ውጤት አስገኝቷል ነው ያሉት።

ዜጎች የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑና ከድህነት ወጥተው ብልጽግናን ማረጋገጥ እንዲችሉ የተደራጀ አቅም መፍጠር ይገባል በሚለው የመደመር መንግስት እሳቤ መሰረትም የህብረት ስራ ማህበራትን የማጠናከር ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።

ለዚህም የህብረት ስራ ማህበራት የፋይናንስ አቅማቸውን አጠናክረው ከድጎማ እንዲላቀቁ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡

ከተረጂነት ለመላቀቅና የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረትም የህብረት ስራ ማህበራት የራሳቸውን አሻራ ማኖር እንዳለባቸው ነው ያሳሰቡት።

የፌዴራል ህብረት ስራ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ሺሰማ ገብረስላሴ በበኩላቸው፤ ህብረት ስራ ማህበራት ላለፉት 65 ዓመታት በተለያዩ ዘርፎች ተደራጅተው ሲንቀሳቀሱ ቆይተዋል ብለዋል።

ሆኖም ግን በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ያበረከቱት አስተዋጽኦ ዝቅተኛ ከመሆኑም ባለፈ አባሎቻቸውን በአግባቡ ለማገዝና ከድጎማና እርዳታ ማውጣት ሳይችሉ መቆየታቸውን ጠቅሰዋል።

መንግስት በአሁኑ ወቅት  ያሉትን 89 ሺህ 164 የህብረት ስራ ማህበራት በአዲስ መልክ በማደራጀት የህግ ማዕቀፎችንና ሌሎች ተያያዥ አሰራሮችን በማሻሻል የፋይናንስ አቅማቸውን የማሳደግ ስራ እየሰራ መሆኑንም አብራርተዋል።  

የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህብረት ስራ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳሙኤል ፎላ እንዳሉት፤ በክልሉ ከ6 ሺህ በላይ የህብረት ስራ ማህበራትና ከ30 በላይ ዩኒየኖች ተደራጅተው እየሰሩ ነው ብለዋል።

ማህበራቱ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በግብርና፣ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ በግብዓት አቅርቦት፣ ገበያን በማረጋጋትና በተለያዩ ዘርፎች ተሰማርተው እየሰሩ መሆናቸውንም በመጠቆም።

ማህበራቱና ዩኒየኖቹ  ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ለማፍራት መቻላቸውንም ነው የገለጹት።

የሲዳማ ክልል ህብረት ስራ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሽመልስ ሀጢሶ በበኩላቸው፤ በክልሉ ያሉት የህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒየኖች በተለያዩ ዘርፎች ተሰማርተው አባላቱንና የክልሉን ማህበረሰብ እያገለገሉ ይገኛሉ ብለዋል።

ማህበራቱ ካፒታላቸውን 7 ቢሊዮን ብር በላይ በማድረስም በክልሉ ኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸውን አስተዋጽኦ እያጎለበቱ መሆናቸውንም ተናግረዋል።

በክልሉ ገበያን ለማረጋጋት የተለያዩ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ እያበረከቱት ያለው አስተዋጽኦ ላቅ ያለ መሆኑንም አስረድተዋል ።

በንቅናቄ መድረኩ ላይ ከሲዳማ፣ ከኦሮሚያና ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተውጣጡ አደራጆች የተሳተፉ ሲሆን መድረኩ ለስምንት ቀናት እንደሚቆይም ተጠቁሟል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም