ምክር ቤቱ የኢትዮጵያ አቭዬሽን ሴኩዩሪቲ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን አፀደቀ - ኢዜአ አማርኛ
ምክር ቤቱ የኢትዮጵያ አቭዬሽን ሴኩዩሪቲ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን አፀደቀ
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018(ኢዜአ)፦ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 15ኛ መደበኛ ስብሰባ የኢትዮጵያ አቭዬሽን ሴኩዩሪቲ አዋጅን ለማሻሻል የቀረበ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ አፅድቋል።
የማሻሻያ አዋጅ ለሁለት አስርት ዓመታት ያህል ስራ ላይ የቆየውን አዋጅ የሚተካ ሲሆን፣ በዘርፉ የታዩ አዳዲስ የደህንነት ስጋቶችንና የቴክኖሎጂ ለውጦችን ግምት ውስጥ ያስገባ መሆኑ ተገልጿል።
በምክር ቤቱ የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈቲህ መሀዲ (ዶ/ር) የረቂቅ አዋጁን ሪፖርትና የውሳኔ ሃሳብ ለምክር ቤቱ አቅርበዋል።
በገለጻቸውም ነባሩ አዋጅ ከ20 ዓመታት በላይ ያገለገለ በመሆኑ በአሁኑ ወቅት በአቭዬሽን ኢንዱስትሪው የሚታዩ ውስብስብ የደህንነት ስጋቶችን ለመከላከል አቅሙ ውስን እንደነበረ አስገንዝበዋል።
አዲሱ አዋጅ የአቭዬሽን ዘርፉን ደህንነት ለማስጠበቅ በርካታ ፋይዳዎች እንዳሉት ጠቅሰው ዘመኑ ያመጣቸውንና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተወሳሰቡ የመጡ ስጋቶችን በብቃት መከላከል የሚያስችል ጠንካራ የሕግ ማዕቀፍ ይፈጥራል ብለዋል፡፡
የአቭዬሽን ደህንነት ፍተሻና የቁጥጥር ሥራዎች ይበልጥ በቴክኖሎጂ የታገዙ፣ ቀልጣፋና አስተማማኝ እንዲሆኑ ያስችላል ያሉት ምክትል ሰብሳቢው የኢትዮጵያን የአቭዬሽን ሴኩዩሪቲ አሠራር ከዓለም አቀፍ የሲቪል አቭዬሽን ድርጅት መለኪያዎችና መስፈርቶች ጋር የተጣጣመ ያደርገዋል ብለዋል።
አዲሱ አዋጅ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕም ሆነ ሌሎች በዘርፉ የተሰማሩ ተቋማት ለዓለም ማህበረሰብ ደህንነቱ የተጠበቀና አስተማማኝ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት እንዲሰጡ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ጠቁመዋል።
አየር መንገዱ በዓለም አቀፍ ደረጃ እያሳየ ያለውን ስኬትና የሀገሪቱን መልካም ገጽታ አጠናክሮ ለማስቀጠል ወቅቱን የዋጀ የሕግ ድጋፍ አስፈላጊ መሆኑንም አክለዋል።
የምክር ቤቱ አባላት በአዋጁ ላይ ሰፊ ውይይት ካደረጉ በኋላ፣ አዋጁ የሀገሪቱን ብሔራዊ ደህንነትና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ያለውን ፋይዳ አድንቀዋል።
ምክር ቤቱ የቀረበለትን የውሳኔ ሃሳብ መርምሮ፣ አዲሱን የኢትዮጵያ አቭዬሽን ሴኩዩሪቲ ማሻሻያ አዋጅ በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል።
ይህ የማሻሻያ አዋጅ ለሁለት አስርት ዓመታት ያህል ስራ ላይ የቆየውንና በ1997 ዓ.ም የወጣውን ነባር አዋጅ ቁጥር 432/1997 የሚተካ ሲሆን፣ በዘርፉ የታዩ አዳዲስ የደህንነት ስጋቶችንና የቴክኖሎጂ ለውጦችን ግምት ውስጥ ያስገባ እንደሆነም ተገልጿል።