ቀጥታ፡

ሀገር አቀፍ ጥናቱ ዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ ለመገንባት መሰረት ይጥላል

ድሬዳዋ፤ሚያዝያ 12/2018(ኢዜአ)፦የመንግስት ሠራተኞች መረጃ ማረጋገጫ ሀገር አቀፍ ጥናት ዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ ለመገንባት  መሰረት እንደሚጥል የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት የድሬዳዋ ቅርንጫፍ ገለፀ።

ለድሬዳዋ አስተዳደርና ለሶማሌ ክልል ሲቲ ዞን የሲቪል ሰርቪስ ተቋማት አመራሮችና ባለሙያዎች የመንግሥት ሠራተኞች የፐርሶኔል መረጃ ማጥራትና ማረጋገጥ ጥናቱን ለመተግበር የሚያስችላቸው ስልጠና ዛሬ ተሰጥቷል።


 

በስልጠናው ላይ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ድሬዳዋ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሙሉጌታ ግርማ ፤ እንደ ሀገር የሚካሄደው የሲቪል ሰርቪስ ሠራተኞች መረጃ ማረጋገጫ ጥናት  የሰው ኃይል ስራ አመራርን ዲጂታላይዝድ ለማድረግ የሚያስችል ነው ብለዋል።

ጥናቱ ትክክለኛ መረጃን በማረጋገጥና የተቋማትን የመረጃ አያያዝ ክፍተት በመሙላት  የሰው ሃብት የመረጃ  አያያዝን ዲጂታላይዝ  ማድረግ   እንደሚያስችል ጠቁመዋል።

ከዚህ በተጨማሪ ጥናቱ ወደ ዘመናዊ እና አውቶሜትድ የሰው ሃይል ስራ አመራር ስርአት ለመሸጋገር ምቹ ሁኔታን  እንደሚፈጥር ነው አቶ ሙሉጌታ የገለፁት።

ለጥናቱ መሳካት አስፈላጊው ዝግጅት እየተጠናቀቀ መሆኑን ጠቅሰው ከዚህ ወር መጨረሻ ጀምሮ ለሚቀጥሉት ሶስት ወራት ጥናቱ እንደሚካሄድ አስታውቀዋል።

የድሬዳዋ አስተዳደር የሲቪል ሰርቪስ እና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሰቦ አህመድ በበኩላቸው፤ ሀገር አቀፉ ጥናት ዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ በመፍጠር የህዝብን መሠረታዊ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በላቀ ተጠያቂነት እና ግልፀኝነት ለመፈፀም ቁልፍ አበርክቶ እንዳለው አንስተዋል።


 

በሚሰበሰበው ትክክለኛ መረጃ ላይ በመመስረት  ሠራተኞች  ለሚያቀርቧቸው ጥያቄዎች መንግስት በፍጥነት ምላሽ ለመስጠትና  ሠራተኞችን ተጠቃሚ ለማድረግ ያስችላል ብለዋል።

በተጨማሪም ሙስናና ብልሹ አሠራሮችን በማስወገድ ከሰው ንክኪ የፀዱ አገልግሎቶችን ተደራሽ በማድረግ የመንግስትና የህዝብ ሃብት ከብክነት ለመከላከል ሚናው የጎላ መሆኑን አስታውቀዋል።

ጥናቱ እንደ ሀገር የተጀመሩትን ውጤታማ የዲጂታል አገልግሎት አሰጣጦችን በማላቅ የብልጽግና ጉዞን ይበልጥ ለማፋጠን ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው የገለፁት ደግሞ የሶማሌ ክልል ሲቲ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ መሐመድ አብዱረህማን ናቸው።


 

አቶ መሐመድ አክለውም፤ ለጥናቱ መሳካት የተመደቡ አስተባባሪዎች ፣ የተቋማት የሰው ሃብት ስራ አመራር ባለሙያዎች እና ኃላፊዎች በላቀ ቁርጠኝነት ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም