ጥረቶቻችን ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለንን አቋም ያሳያሉ -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
ጥረቶቻችን ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለንን አቋም ያሳያሉ -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፡- ጥረቶቻችን የበለጠ ጽኑ፣ተወዳዳሪ እና አካታች ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለንን አቋም እና የመተግበር ዐቅም ያሳያሉ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ የሥራ ዘመኑን ሦስተኛ የ100 ቀናት የመንግሥት ሥራ አፈፃፀም ከዘጠኝ ወራት አጠቃላይ አፈፃፀም ጎን ለጎን መገምገም ጀምረናል ብለዋል።
ለእድገት አመቺ ካልነበረው እና በደካማ የተቋማት እና የፖለቲካ ማዕቀፍ፣ በታጠረ የግል ዘርፍ ተሳትፎ እንዲሁም ውጤታማ ባልነበረ የቁጥጥር ከባቢ ከሚገለጠው የኢኮኖሚ መልክ ወጥተናል ሲሉም ገልጸዋል።
የግሉ ዘርፍ ደካማ ውድድር ውስጥ ነበር ሲሉም አውስተዋል።
በመንግሥት ሥር የነበሩ በርከት ያለ ቁጥር ያላቸው የንግድ ተቋማትም ከፍ ባለ የዕዳ ሸክም ተዘፍቀው ከዐቅም በታች ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ይታወቃል ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
ምርታማነት አሽቆልቁሎ ኢኮኖሚውም ለአየር ንብረት ለውጥ በከፍተኛ ደረጃ ተጋላጭ የነበረውን ነባራዊ ሁኔታ ምላሽ በሚሰጥ አዲስ ገቢር ነበብ የፖለቲካ ኢኮኖሚ መንገድ ቀይሰናል ሲሉም አስታውቀዋል።
የቀየስነው አዲሱ የኢኮኖሚ አካሄድ በአጭር ጊዜ ትግበራ ጠንካራ ባለሁለት አሃዝ የእድገት ሂደትን አስመዝግቧል ብለዋል በመልዕክታቸው።
በአሁኑ ወቅት ኢኮኖሚያችን በ9 ነጥብ 2 በመቶ እያደገ ይገኛል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ይኽ እድገት በመጪው ዓመት ወደ10 ነጥብ 2 በመቶ እንደሚያድግ እንጠብቃለን ሲሉ አመላክተዋል።
በየዘርፉም የታቀዱ ግቦቻችንን ለማሳካት ከፍ ባለ ትጋት ቀጥለን፤ በግብርና 7 ነጥብ 9 በመቶ፣ በኢንዱስትሪ 13 ነጥብ 2 በመቶ፣ በአገልግሎት 9 ነጥብ 3 በመቶ ዕድገቶች ሳይቆራረጡ የሚከናወኑ ይሆናል በማለት ገልጸዋል።
እነዚህ ጥረቶች የበለጠ ጽኑ፣ተወዳዳሪ እና አካታች ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለንን አቋም እና የመተግበር ዐቅም ያሳያሉ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)።