የሰው ሰራሽ አስተውሎት የጤና ኤክስቴንሽን ሠራተኞችን ስራ በመደገፍ ረገድ ከፍተኛ ለውጥ እያመጣ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የሰው ሰራሽ አስተውሎት የጤና ኤክስቴንሽን ሠራተኞችን ስራ በመደገፍ ረገድ ከፍተኛ ለውጥ እያመጣ ነው
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የጤና ኤክስቴንሽን ሠራተኞችን ስራ በመደገፍ ረገድ ከፍተኛ ለውጥ እያመጣ እንደሚገኝ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።
የጤና ሚኒስቴር በሰው ሰራሽ አስተውሎት (Al) በመደገፍ ለጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎች የስራ አጋዥ ተግባራትን በማጎልበት በተመረጡ ወረዳዎች በተደረገው የሙከራ ትግበራ ማስተዋወቅ እና እስካሁን ያለውን ሂደት የሚገመግም መድረክ አካሂዷል።
በጤና ሚኒስቴር የማህበረሰብ ተሳትፎና የመጀመርያ ደረጃ ጤና ክብካቤ መሪ ሥራ አስፈፃሚ እስራኤል አታሮ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ሚኒስቴሩ ሰው ሰራሽ አስተውሎት በመጠቀም የተሻለ የጤና አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ እየሰራ ይገኛል።
በዲጂታል ቴክኖሎጂ መረጃ አያያዝ ማጠናቀር እንዲሁም በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ ህክምና አሰጣጥ ስራዎችን ማከናወን የዚሁ አካል መሆናቸውን አመልክተዋል።
የትግበራ ምዕራፍ ላይ የምትገኘው 'ሀዋ' የተሰኘችው የሰው ሰራሽ አስተውሎት የጤና ኤክስቴንሽን ሠራተኞችን ስራ በመደገፍ ረገድ ትልቅ ለውጥ ማምጣት ታስችላለች ብለዋል።
ይህ አዲስ አሰራር ባለሙያዎች በታብሌት በመታገዝ አዳዲስ የበሽታ ምልክቶችን በፍጥነት እንዲለዩና የወረቀት ፓኬጆችን ወደ ዲጂታል በመቀየር መረጃን በቀላሉ እንዲያስተዳድሩ ያግዛል ብለዋል።
በሰው ሰራሽ አስተውሎት (Al) የተደገፈ የህክምና አገልግሎት አሰጣጥን ለማጠናከር ካሁን ቀደም ተግባራዊ ከተደረገባቸው ወረዳዎች በተጨማሪ ተደራሽ ባልተደረገባቸው አካባቢዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልፀዋል።
ይህ ቴክኖሎጂ የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎች መደበኛ ሥራቸው ላይ የተሻለ እገዛ በማድረግ ውጤታማ አገልግሎት እንዲሰጡ ያስችላል ነው ያሉት፡፡
የኤክስቴንሽን ባለሙያዎች መረጃን በዲጂታል እንዲይዙና አዳዲስ የበሽታ ምልክቶችን ለይተው ለቀጣይ ህክምና ማስተላለፍ እንደሚያስችል ተጠቅሷል።
እንዲሁም ከጤና ኬላዎች ወደ ጤና ጣቢያዎች የሚደረገውን አላስፈላጊ ሪፈራልና የታካሚዎች እንግልት ለመቀነስና በሰው ሰራሽ አስተውሎት (Al) ታካሚዎች በአቅራቢያቸው በሚገኙ የጤና ኬላዎች አፋጣኝ ህክምናና እፎይታ እንዲያገኙ ያስችላል ተብሏል።
በ'ላስት ማይል ኸልዝ' ከፍተኛ የፕሮግራም ሥራ አስኪያጅ ሩት ድሪባ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የጤና ኤክስቴንሽን አጋዥ የሰው ሠራሽ አስተውሎት መርጃው ለአንድ ዓመት ተኩል ያህል በሙከራ ደረጃ መቆየቱን ተናግረዋል።
ሰው ሰራሽ አስተውሎት የጤናውን ዘርፍ አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት ለማስፋት ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው ገልፀው፤ በተጨማሪም እንደሃገር የተያዘውን ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን እውን ለማድረግ ትልቅ ድርሻ ይኖረዋል ብለዋል።