ቀጥታ፡

የታዳሽ ኃይል የልማት ስኬቶች የአካባቢ ደኅንነት ጥበቃ የድል ማሕተሞች ናቸው 

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል የልማት ስኬቶች የአካባቢ ደኅንነት ጥበቃን በማረጋገጥ የብልፅግናን ጉዞ የሚያፋጥኑ የድል ማሕተሞች መሆናቸውን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ገለጹ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ሄጦሳ ወረዳ ኢተያ አካባቢ የተገነባውን የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ በዛሬው ዕለት መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። 


 

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ በዚሁ ወቅት፣ ኢትዮጵያ ከውሃ፣ ከንፋስ፣ ከፀሐይ፣ ከጂኦተርማል እንዲሁም ከባዮ ጋዝና ታዳሽ ኃይል አማራጮች እምቅ አቅም እንዳላት ገልጸዋል።

በዚህም እያደገ የመጣውን የኃይል ፍላጎት አስተማማኝና ቀጣይነት ባለው መልኩ ለመመለስ የሚያስችሉ ተግባራት እየተሰሩ መሆናቸውን አመላክተዋል።

ዛሬ የተመረቀው የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ የዚሁ አካል መሆኑን አንስተው፤ ፕሮጅክቱ በ29 ተርባይኖች 100 ሜጋ ዋት ኃይል የማመንጨት አቅም ያለው ነው ብለዋል።

ይህም ሀገሪቱ ከንፋስ ኃይል የምታገኘውን የማመንጨት አቅም ወደ 504 ሜጋ ዋት በማሳደግ ተቋሙ የኃይል ስብጥርን ለማመጣጠን የሰጠውን ትኩረት የሚያግዝ ነው ብለዋል፡፡


 

 

የፕሮጀክቱ ወደ ስራ መግባት ተደማሪ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦት እንዲኖር የሚያስችል መሆኑን በመግለጽ፤ የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል የልማት ስኬቶች የአካባቢ ደኅንነት ጥበቃን በማፋጠን የብልፅግናን ጉዞ የሚያፋጥኑ የድል ማሕተሞች መሆናቸውን ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ የዴንማርክ አምባሳደር ሱን ክሮግስትራፕ በበከላቸው እንደገለጹት፤ የንፋስ ኃይል ማመንጫው ለዘላቂ ኢኮኖሚ እድገትና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ወሳኝ ነው፡፡


 

ኢትዮጵያና ዴንማርክ በዚህ ረገድ በጋራ እየሰሩ መሆኑን አንስተው፤ የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ይህን የሚያጠናክር ከመሆኑም ባለፈ ለቀጣይ ታዳሽ ኃይል ኢንቨስትመንት መሰረት የሚጥል መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ( ዶ/ር) አነሳሸነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ለዓለም አርአያ የሆነ ተግባር መሆኑን አንስተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም