ቀጥታ፡

የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ጸጋን የመለየት፣ የማልማትና ወደ ሀብት የመቀየር ትልቅ ማሳያ ነው

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ጸጋን የመለየት፣ የማልማትና ወደ ሀብት የመቀየር ትልቅ ማሳያ መሆኑንና ለወሎ የብልጽግና ተስፋ እንደሆነ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሣሽነት እና በ"ገበታ ለትውልድ" መርሐ ግብር የተገነባውን የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ዛሬ በታሪካዊቷ የሐይቅ ከተማ ተገኝተው ሥራ ያስጀመሩት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በምርቃቱ ሥነ ሥርዓት ላይ ከአካባቢው ማኅበረሰብና ከአፋር ወንድሞች ጋር በአንድነት በመገኘታቸው የተሰማቸውን ታላቅ ደስታ ገልጸዋል።


 

ወሎ የኅብር ምልክት መሆኗን የጠቀሱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በዕለቱ ከአፋር ወንድሞች ጋር የታየው አብሮነት የኢትዮጵያን ውበትና ወንድማማችነት ይበልጥ የገለጠ መሆኑን አመልክተዋል።

ይህ ፕሮጀክት ከግንባታው ጅማሮ እስከ ፍጻሜው የመደመር ዕሳቤ በተግባር የታየበት መሆኑን ገልጸው የመንግሥት ሐሳብ፣ የባለሀብቱ ታታሪነት እና የሕዝቡ ትጋት የተሰባጠረበት ድንቅ ውጤት መሆኑን አብራርተዋል።

ፕሮጀክቱ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ሌት ተቀን ጥበቃ ላደረጉ የመከላከያ፣ የፖሊስ እና የሚሊሻ አባላት፣ እንዲሁም ለአካባቢው አመራርና ሕዝብ የላቀ ምስጋና አቅርበዋል።

ባለሀብቱ አቶ በላይነህ ክንዴ ሪዞርቱን ውብ አድርገው ከመገንባት ባለፈ፣ ጫትን በምርጥ የአትክልትና ፍራፍሬ ዝርያ በመተካት ለውጥ በተግባር እንደሚመጣ ማሳየታቸውን ገልጸዋል።


 

በተጨማሪም ባለሀብቱ ለሐይቅ ከተማ የገነቡት ትምህርት ቤት ለትውልድ የሚተርፍ ተግባር መሆኑን በመልዕክታቸው ላይ ጠቅሰዋል።

ዛሬ የታየው ልማት የሰላም ውጤት መሆኑን ያመለከቱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና ወጣቶች ሰላማቸውን አጥብቀው እንዲጠብቁ አደራ ብለዋል።

በአንድነት እና በትጋት ከተሠራ ቀጣናው የዕድገትና የብልጽግና መዳረሻ መሆኑ እንደማይቀርም አጽንኦት ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም