የዓለም ባንክ እና ጣልያን ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም ድጋፋቸውን እንደሚያጠናክሩ ገለጹ - ኢዜአ አማርኛ
የዓለም ባንክ እና ጣልያን ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም ድጋፋቸውን እንደሚያጠናክሩ ገለጹ
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም ባንክ እና ጣልያን ለኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ድጋፍ ማድረጋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታወቁ።
በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ፣ የሶስትዮሽ አጋርነትን ይበልጥ ለማሳደግ ያለመ ከፍተኛ ምክክር ከዓለም ባንክ እና ከጣልያን ልዑካን ቡድን ጋር አካሂዷል።
የውይይቱ ዋነኛ ትኩረት የኢትዮጵያን ቀጣይ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም ለመደገፍ በሦስቱ ወገኖች መካከል ያለውን ትብብር ማጠናከር ነው።
ሀገሪቱ ቅድሚያ ከምትሰጣቸው የልማት ጉዳዮች ጋር የተጣጣመ፣ ወቅቱን የጠበቀና አስተማማኝ የፋይናንስ ድጋፍ ማሰባሰብ በሚቻልባቸው መንገዶች ላይም መክረዋል።
የኢትዮጵያ ልዑክ በቅርቡ የተመዘገቡ የማክሮ ኢኮኖሚ ስኬቶችን ያብራራ ሲሆን፤ መንግሥት የጀመረውን የማሻሻያ እንቅስቃሴ ለማስቀጠል፣ የፋይናንስ ሥርዓትን (Fiscal Discipline) ይበልጥ ለማስጥበቅና ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ ያለውን ጽኑ አቋም በድጋሚ አረጋግጧል።
በውይይቱ የልማት አጋሮች የሚያደርጉት ድጋፍ የተቀናጀ መሆን ያለው ጠቀሜታ አጽንኦት ተሰጥቶበታል።
ይህም የሚደረገው ድጋፍ የሚፈለገውን ውጤት እንዲያመጣና የሀብት አጠቃቀም ውጤታማ እንዲሆን የሚያስችል እንደሆነ ተመላክቷል።
የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያውን ከማገዝ ባለፈ፣ ኢትዮጵያ ተለዋዋጭና ውስብስብ የሆነውን የዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ሁኔታ ተቋቁማ እንድትሻገር የሚያስችሉ የተቀናጁ የድጋፍ ማዕቀፎች ላይ ውይይት ተካሂዷል።
የጣልያን ልዑክ በበኩሉ ኢትዮጵያ ለምታደርገው የልማት ጥረት ያለውን አጋርነት በድጋሚ ያረጋገጠ ሲሆን፣ በተለይም በሁለትዮሽ ትብብር እና ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ማዕቀፎች ጋር በተጣጣመ መልኩ ድጋፉን እንደሚያጠናክር ገልጿል።
በተመሳሳይ ዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም ቀጣይነት ስላለው ድጋፍ በመግለጽ፣ ውጤታማ የፋይናንስ ትብብርን ለማሳደግ ከአጋሮች ጋር በቅርበት ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን አሳውቋል።
ወቅታዊ የኢኮኖሚ ተግዳሮቶችንና የፋይናንስ ውስንነቶችን በዘላቂነት ለመወጣት ጽኑ አጋርነትና የጋራ ጥረት አስፈላጊ መሆኑንም በውይይታቸው አጽንኦት ሰጥተዋል።
ከዚህም ባሻገር ተጨባጭ የልማት ውጤቶችን ለማስመዝገብ ዘላቂ የፖሊሲ ቅንጅት፣ የተቀናጀ ተግባቦት እና የጋራ ተጠያቂነት አስፈላጊ መሆናቸው በውይይቱ ወቅት ተመልክቷል።
በሦስቱ ወገኖች መካከል ያለውን ጥምረት ይበልጥ ለማጠናከርና የተቀናጀ የትብብር ማዕቀፍን ለማዘጋጀት የሚደረገውን ጥረት ለማሳለጥ በውይይቱ የጋራ ስምምነት ላይ ተደርሷል።
ኢትዮጵያ ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ የኢኮኖሚ ጥንካሬና ዕድገትን ለማረጋገጥ ወሳኝ የሆኑ መዋቅራዊ ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ለማድረግ ያላትን ጽኑ አቋም በድጋሚ ማረጋገጧን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።