በሲዳማ ክልል በቴክኖሎጂ በመታገዘ ገቢን በአግባቡ ለመሰብሰብ ተችሏል - ባለስልጣኑ - ኢዜአ አማርኛ
በሲዳማ ክልል በቴክኖሎጂ በመታገዘ ገቢን በአግባቡ ለመሰብሰብ ተችሏል - ባለስልጣኑ
ሀዋሳ፤ ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል በቴክኖሎጂ በመታገዘ ገቢን በአግባቡ ለመሰብሰብ መቻሉን የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን አስታወቀ።
የባለስልጣኑ ምክትል ዳይሬክተርና የደንበኞች አገልግሎት፣ የታክስ አወሳሰንና አሰባሰብ ዘርፍ ኃላፊ ሙላት ዮሴፍ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ በክልሉ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱን በማዘመን ውጤታማ ስራዎችን ለመስራት እየተቻለ ነው።
የክልሉን ገቢ ለማሳደግ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ሲሆን ዘመናዊ የአከፋፈል ስርዓት (የኢ-ፋይልንግና የኢ-ፔይመንት) አሰራር መዘርጋቱ ለውጤቱ አስተዋጽኦ ከማድረግ ባለፈ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት አስችሏል ነው ያሉት።
በተለይም ከእጅ ንክኪ ነጻ የሆነ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱን በማዘመን ክልሉ የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ ለመሰብሰብ አስችሏል ብለዋል።
በተለይም ከፍተኛ ግብር ከፋይ የሆኑ ከ626 በላይ የመንግስትና የግል ተቋማት ሙሉ በሙሉ ግብራቸውን የሚያሳውቁበትና የሚከፍሉበት የኤሌክትሮኒክስ አሰራር ነው የተዘረጋው ብለዋል።
በተያዘው በጀት ዓመት ለመሰብሰብ ከታቀደው ከ 21 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ውስጥ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ15 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለማግኝት መቻሉን ገልፀዋል።
የተሰበሰበው ገቢ የእቅዱን 94 በመቶ ለማሳካት ያስቻለ ሲሆን ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ 5 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው ገልጸዋል፡፡
ገቢው ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች የተሰበሰበ መሆኑንም ተናግረዋል።
በፌዴራል ደረጃ የተሻሻለው አዲሱን የግብር አዋጅ ጨምሮ ሌሎች የታሪፍ ማሻሻያዎች መደረጋቸው የገቢ አቅምን ለማሳደግ የራሱ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ብለዋል፡፡
በዚሁ ወቅት የቁጥጥርና የአሰራር ስርዓትን በማጠናከር ለታክስ ህግ ተገዥ ባልሆኑ ከ400 በላይ ግብር ከፋዮችን ጨምሮ በክልሉ ሰባት ከተሞች ደረሰኝ ሳይቆርጡ በሚሰሩ ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል፡፡
በቀሪ ጊዜትም የተቀመጠውን እቅድ ለማሳካት ወቅታዊ ሁኔታን ያገናዘበ የክትትልና የቁጥጥር ስራ እንደሚከናወን ገልጸዋል፡፡
በሃዋሳ ከተማ ግብር ከፋይ የሆኑት መምህር ተስፋዬ አበበ፤ በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብር አከፋፈል ስርዓት መኖሩ ሂደቱን ቀልጣፋ እንዳደረገው ገልፀዋል።
ግብርን በታማኝነት መክፈል ሀገራዊ ግዴታ በመሆኑ ኃላፊነታቸውን በተገቢው እየተወጡ መሆኑን አመልክተው ድርጅታቸው ላለፉት ተከታታይ ዓመታት የክልሉ ከፍተኛ ግብር ከፋይ በመሆን ሽልማት ማግኘቱን ተናግረዋል።