ቀጥታ፡

ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ የኢኮኖሚ ልብ ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፡- ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ማደግ ለሚያስብ ሀገር ሁሉ በጣም ወሳኝ እና የኢኮኖሚ ልብ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) “የሉዓላዊነት ልብ” በሚል ርዕሰ ጉዳይ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ጋር ቆይታ አድርገዋል።

በቆይታቸውም፤የመደመር መንግሥት መጽሐፍ በፖለቲካና በኢኮኖሚ መካከል ሚዛን መጠበቅ፣ ፖለቲካል ኢኮኖሚን በትክክል መግራትና መረዳት አስፈላጊ ነው ብሎ በሚዛን የሚነሳ መሆኑን አስረድተዋል።

አንዱ ገዝፎ አንደኛው ያነሰ እንደሆነ፤ የሚፈለገውን ሥር ነቀል ለውጥ ማምጣት ያስቸግራል ሲሉም አመላክተዋል።

ለዚህ ነው የመደመር መንግሥት ሚዛን ጠብቆ ድርሻቸው ሳይዛባ አንዱ ለአንደኛው መከታ ተሸካሚ ሆኖ በጋራ ብልጽግናን ማረጋገጥ እንዲችሉ በትኩረት የተሠራው ብለዋል።

ይህ እንዳለ ሆኖ የብዙ መንግሥታት የእኛም ትኩረት ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ላይ የሆነበት ዋናው ምክንያት፤ኢንዱስትሪ ለመለወጥ (ለማደግ) ለሚያስብ ሀገር ሁሉ በጣም ወሳኝ ነገር ስለሆነ ነው ብለዋል።

አክለውም፤ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ የኢኮኖሚ ልብ መሆኑን አስገንዝበዋል።

አንድ ሰው ልቡ ካልሠራ ሌላው አካላቱ ጤነኛ ቢሆንም ውጤታማ እንደማይሆን ሁሉ፤ ኢኮኖሚን ኢኮኖሚ የሚያደርገው የኢኮኖሚ ልብ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም