በአማራ ክልል በቴክኖሎጂ የታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስርዓትን በመተግበር ረገድ የተገኘው ውጤት ልምድ የሚወሰድበት ነው - ኢዜአ አማርኛ
በአማራ ክልል በቴክኖሎጂ የታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስርዓትን በመተግበር ረገድ የተገኘው ውጤት ልምድ የሚወሰድበት ነው
ባህርዳር ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡- የአማራ ክልል በቴክኖሎጂ የታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስርአትን በመተግበር ረገድ የተገኘው ውጤት ልምድና ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑ ተገለጸ።
የአፋር ክልል ገቢዎች ቢሮ፤ የከተማ አስተዳደሮችና ዞኖች የስራ ሀላፊዎች ቡድን ከአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ልምድ ወስደዋል።
የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮም በቴክኖሎጂ በታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስራው ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 66 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ መቻሉን አስታውቋል።
የአፋር ክልል ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ አወል አብዲ በጉብኝቱ ላይ እንደገለጹት፤ የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ በአሰራር፣ በአደረጃጀትና በቴክኖሎጂ የተደራጀው አሰራሩ ጥሩ ልምድ የሚወሰድበት ነው።
የልምድ ልውውጡም በአፋር ክልል ገቢ አሰባሰብ ስራው ላይ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
ዘመናዊ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂን በመተግበር ፈጣን፣ ግልጽና ተጠያቂነት ያለው አሰራር ለማስፈን የተደረገው ጥረት ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ ለመሰብሰብ መሰረት መሆኑንም ለመገንዘብ መቻላቸውንም ገልጸዋል።
የክልሉን ህዝብ የልማትና የሰላም ፍላጎት ለማሟላት የሚቻለው ያለውን ሃብት በአግባቡ በመለየት በተገቢው መሰብሰብ ሲቻል መሆኑንም ገልፀዋል።
የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አብዱሙሳ ሁሴን በበኩላቸው፤ የአማራ ክልል በገቢ አሰባሰብ ዘርፍ እያከናወነ ያለው ሁሉን አቀፍ ተግባራትን ለመገንዘብ መቻላቸውን ገልፀዋል።
አሁን ላይ በአሰራር፣ በቴክኖሎጂ አጠቃቀምና ትግበራ እንዲሁም በህግ ማእቀፍ ዝግጅት ያገኙትን ልምድ ወደ ከተማ አስተዳደራቸው ወስደው በመተግበር ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ ለልማት ለማዋል ቁርጠኝነትን እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል።
የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ሃላፊ መንገሻ ፈንታው (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት 66 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰብ ተችሏል።
በተለይም የ'ኤሌክትሮኒክስ ታክስ አድሚኒስትሬሽን ሲስተም' ተግባራዊ በመደረጉ ትልቅ ውጤት ለማስመዝገብ እንደተቻለም ጠቅሰዋል።
በተጨማሪም ለባለሙያዎች ግንዛቤ በመፍጠር በተሟላ መንገድ እስከታች ድረስ እንዲተገበር መደረጉን አስገንዝበዋል።
ይህም ማሕበረሰቡ መብትና ግዴታውን በመገንዘብ የሚጠበቅበትን ግብር በፍትሃዊነት፣ በግልጽነትና ከብልሹ አሰራር በጸዳ መልኩ እንዲከፍል እድል የፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል።