ቀጥታ፡

የመደመር ዕሳቤ ዘመናዊ የአመራረት ሥርዓት ተረጅነትን በማስቀረት የግብርና ምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ ነው

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- የመደመር ዕሳቤ ዘመናዊ የአመራረት ሥርዓት ተረጅነትን በማስቀረት የግብርና ምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ገለጹ። 

በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዳማ ከተማ የውይይት መድረክ ተካሄዷል። 


 

የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር)፥ የልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር የዜጎችን የምርታማነት ሽግግር እያፋጠነ ነው ብለዋል። 

በዚህም የልማታዊ ሴፍቲኔት ተጠቃሚ ለነበሩ ዜጎች የሚደረገው የመስኖ ቴክኖሎጂና የግብዓት አቅርቦት ድጋፍ ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ማሸጋገር እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። 

ይህም የአካባቢ ጥበቃና ሥነ-ምኅዳር ግንባታን በማጠናከር የኢትዮጵያን የዘመናት አሳፋሪ የተረጅነት ታሪክ መስበር እንዳስቻለ አንስተዋል። 

የዜጎች የሴፍቲኔት ተጠቃሚነት የምርቃት መርሃ ግብር በቀላሉ የሚታይ ሳይሆን ከተረጅነት ወደ ምርታማነት የሚደረግ ወሳኝ የልማት ሽግግር ነው ብለዋል። 

የመደመር ዕሳቤና ዘመናዊ የአመራረት ሥርዓት ተረጅነትን በማስቀረት የግብርና ምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል።

የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር አማካሪ ጥላሁን በጅቷል (ዶ/ር)በበኩላቸው፥ አንዳንድ ሀገራት ዕምቅ የመልማት አቅምና ጸጋ ኖሯቸው ሳለ ድህነትን እጣ ፋንታቸው አድርገው እንደሚኖሩ አንስተዋል። 


 

ኢትዮጵያም በሁሉም መስክ ዕድገትና ብልፅግናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ የብዝኅ ጸጋዎች ባለቤት ሆና ሳለ ከድኅነት ጋር ተቆራኝታ እንደቆየች ገልጸዋል። 

በዚህ መነሻነትም ከሀገራዊ ለውጡ ማግስት የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል የተተገበሩ የፖሊሲ እርምጃዎች የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል አቅም እየተፈጠሩ ነው ብለዋል። 

በቀጣይም የዜጎችን የሥራ ባህል በመገንባት የብሔራዊ ሀፍረት መነሻ የሆነውን የተረጅነት ታሪክ ለማስቀረት በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። 

የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ጌቱ ገመቹ፥ በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የክልሉን ብዝኅ የግብርና ምርታማነት ምኅዳር በመጠቀም በርካታ ዜጎች ከድኅነት ወደምርታማነት እንዲሸጋገሩ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። 


 

በግብርናው መስክ አርሶና አርብቶ አደሩ የተፈጠረው የሥራ ባህል ለውጥም የምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። 

በቀጣይም የተቋማትን ጠንካራ ቅንጅት በማስቀጠል ሁለንተናዊ የምግብ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። 

የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ እታገኘሁ አደመ፥ የልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር የአካባቢ ደህንነትን በመጠበቅ የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ ማድረጉን ገልጸዋል። 


 

ይህም የደንና የፍራፍሬ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የዜጎችን ገቢ የማመንጨት አቅም በማሳደግ ከተረጂነት ወደ አምራችነት እያሸጋገረ ነው ብለዋል። 

በመስኖ መሠረተ ልማት መርሃ ግብርም በርካታ ዜጎች የምግብ ዋስትናቸውን እንዲረጋገጥ እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም