ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ወታደራዊ የኢንዱስትሪና የቴክኖሎጂ ትብብራቸውን ለማሳደግ ተስማሙ - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ወታደራዊ የኢንዱስትሪና የቴክኖሎጂ ትብብራቸውን ለማሳደግ ተስማሙ
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ወታደራዊ የኢንዱስትሪና የቴክኖሎጂ ትብብራቸውን ለማሳደግ ተስማምተዋል።
የመከላከያ ሚኒስትር አይሻ መሐመድ (ኢ/ር) ከላይቤሪያ ሪፐብሊክ መከላከያ ሚኒስትር ብርጋዲየር ጄኔራል ጄራልዲን ጃኔት ጆርጅ ጋር በአዲስ አበባ ተወያይተዋል።
በዚሁ ወቅትም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ወታደራዊ ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር በሚቻልባቸው ስትራቴጂካዊ ጉዳዮች ላይ መክረዋል።
ሚኒስትር አይሻ (ኢ/ር) ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ የአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት መሆናቸውን አስታውሰው፤ ይህ የታሪክ ትስስር አሁን ላለው ወታደራዊ ትብብር ጠንካራ መሠረት የሚጥል መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በወታደራዊ ኢንዱስትሪና በዐቅም ግንባታ ዙሪያ በትብብር ለመሥራት ኢትዮጵያ ዝግጁ መሆኗንም አረጋግጠዋል፡፡
ብርጋዲየር ጄኔራል ጄራልዲን ጃኔት ጆርጅ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የሰላም ማስከበር ስምሪትን ጨምሮ በወታደራዊ ሳይንስ እና በዘመናዊ መከላከያ ግንባታ ያካበተችው ተሞክሮ ለላይቤሪያ ትልቅ ትምህርት የሚገኝበት መሆኑን ገልፀዋል።
ላይቤሪያ ከኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ሰፊ ልምድ የመቅሰም ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላትም አስታውቀዋል።
በተለይም በስልጠና እና በቴክኒክ ዘርፎች የሁለቱን ሀገራት ወታደራዊ ትብብር ይበልጥ ለማሳደግ እንደሚሠሩ መናገራቸውን የመከላከያ ኦንላይን ሚዲያ ለኢዜአ የላከው መረጃ ያመላክታል።