ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች ለመላው አፍሪካ ኩራት ናቸው - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች ለመላው አፍሪካ ኩራት ናቸው
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ) ፦ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች ለመላው አፍሪካ ኩራት ናቸው ሲሉ የላይቤሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳራ ቤይሶሎው ኒያቲ ገለፁ።
ኢትዮጵያ በውጭ አገልግሎት አሰጣጥ (outsourcing) እና በፈጠራ ዘርፍ በአህጉሪቱ ተወዳዳሪና የማይበገር አቅም እየገነባች መሆኑንም ገልጸዋል።
የላይቤሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳራ ቤይሶሎው ኒያ የተመራ ልዑክ የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርክን ጎብኝቷል።
ሚኒስትሯ ሳራ ቤይሶሎው ኒያ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ዘርፍ የታዩ ለውጦች ለመላው አፍሪካ ኩራት ናቸው።
ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ያላቸውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ያላቸውን ፍላጎትም ገልጸዋል።
በተለይም በቴክኖሎጂ፣ በግብርና እና በትምህርት ዘርፎች ላይ በትብብር በመሥራት የሁለቱን አገራት ሕዝቦች ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚገባም አስረድተዋል።
አፍሪካ ያላትን ሰፊ የሰው ሀይል በተለይም የወጣቶችን ኃይል በአግባቡ ለጠቀም በ"ደቡብ-ደቡብ" አገራት መካከል ያለው ትብብር ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመዋል።
በአፍሪካ ደረጃ በጋራና በቅንጅት ከተሰራ አህጉሪቷን በልማት ማሳደግ እንደሚቻል አጽንኦት ሰጥተዋል።
በአይ ሲቲ ፓርክ የተመለከቷቸውን የዳታ ማዕከላት አስመልክተው ኢትዮጵያ በውጭ አገልግሎት አሰጣጥ (outsourcing) እና በፈጠራ ረገድ በአህጉሪቱ ተወዳዳሪና የማይበገር አቅም እየገነባች መምጣቷን ገልፀዋል።
በተለይም ወጣቶች አዳዲስ ግኝቶችን እንዲያመነጩ በፓርኩ ውስጥ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ለሌሎች አገራት ምሳሌ የሚሆን ነው ብለዋል።
በተለይም የዳታ ማዕከሉ አፍሪካ የራሷን መረጃ በራሷ አቅም የመያዝ ብቃት እንዳላት ማሳያ መሆኑንም ገልጸው፤ ላይቤሪያ ከኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ተሞክሮ በመቀመር የራሷን የዳታ ማከማቻ ማዕከል ለመገንባት ያላትን ፍላጎት አረጋግጠዋል።
ጉብኝቱ በሁለቱ ጥንታዊ አፍሪካዊ አገራት መካከል ያለውን ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ተግባራዊ የኢኮኖሚ እና የቴክኖሎጂ አጋርነት የሚያሸጋግር መሆኑ ተመላክቷል።
በላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ የተመራ ልዑክ ለስራ ጉብኝት ትናንት ማምሻውን አዲስ አበባ መግባቱ ይታወቃል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ አቀባበል አድርገውላቸዋል።