ቀጥታ፡

የኮደርስ ስልጠና ቀልጣፋና ዘመናዊ የሕዝብ አገልግሎት መስጠት አስችሏል

ጅማ፤ ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡- በጅማ የኮደርስ ስልጠና የወሰዱ የመንግሥት ሠራተኞች ቀልጣፋና ዘመናዊ የሕዝብ አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ እያገዛቸው መሆኑን ገለጹ።

የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ የሆነው የ 5 ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በጅማ ከተማ በሚገኙ የተለያዩ የመንግሥት ተቋማት ሠራተኞች ዘንድ ትልቅ መነቃቃትን እየፈጠረ መሆኑ ተመልክቷል።

ስልጠናው የሠራተኞችን የዲጂታል ክህሎት በማሳደግ፣ ቀልጣፋና ዘመናዊ የሕዝብ አገልግሎት ለመስጠት ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑም ተገልጿል። 

ሰራተኞቹ እንደሚናገሩት፤ የስልጠናው መርሃ ግብር በሥራቸው ላይ ተጨማሪ ዕውቀትና ክህሎት ጨምሮላቸዋል።

በኢፌዲሪ የግል ድርጅቶች ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር የጅማ ዲስትሪክት ሠራተኞች የሆኑት ምህረት ካሳ እና ቁምነገር ወርቅዬ፣ ተቋሙ የኮምፒውተርና የኢንተርኔት አገልግሎትን ምቹ በማድረጉ የተለያዩ ኮርሶች መውሰዳቸውን ይናገራሉ። 

ከስልጠናው በኋላም በተቋሙ ውስጥ ለሚሰሩት ሥራ ትልቅ እገዛ ማድረጉን ገልጸዋል።

በተጨማሪም ዓለም አቀፍ የሥልጠና ሰርተፊኬት ማግኘት መቻላቸውን ጠቅሰው፣ ሌሎች ሠራተኞችም ዕድሉን እንዲጠቀሙበት መክረዋል።

የዲስትሪክቱ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መስፍን መሸሻ በበኩላቸው፣ ከተቋሙ 140 ሠራተኞች መካከል 70 በመቶ የሚሆኑት ስልጠናውን መውሰዳቸውን ገልጸዋል። 


 

ቀሪዎቹም ስልጠናውን እንዲያገኙ የግንዛቤ ማስጨበጥና የቴክኖሎጂ አቅርቦትን የማመቻቸት ሥራ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።

በጅማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ውስጥ የሚሰሩት ሙስሊማ አወል እና መሐመድ ኃይደር፣ አገልግሎቶች ወደ ዲጂታል እየተቀየሩ ባለበት በዚህ ወቅት ስልጠናው እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። 

"ከመደበኛ ሥራችን ጎን ለጎን ስልጠናውን መውሰዳችን ሥራችንን ይበልጥ ለማቀላጠፍና ለማስፋት እያገዘን ነው" ብለዋል።


 

የማዕከሉ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አብዲ ሰለሞን እንደገለጹት፣ ከተቋሙ 104 ሠራተኞች መካከል 80 ያህሉ ስልጠናውን አጠናቅቀው ሰርተፊኬት ወስደዋል። 

ስልጠናው ሠራተኞች ለማኅበረሰቡ የሚሰጡት አገልግሎት በእውቀት ላይ የተመሠረተና ፈጣን እንዲሆን እያስቻለ መሆኑንም አክለዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም