በክልሉ በአምራች ኢንዱስትሪዎች ለተኪና ወጪ ንግድ ምርቶች እድገት ትኩረት ተሰጥቶ ተከናውኗል - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ በአምራች ኢንዱስትሪዎች ለተኪና ወጪ ንግድ ምርቶች እድገት ትኩረት ተሰጥቶ ተከናውኗል
ባህርዳር፤ ሚያዚያ 5/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት በአምራች ኢንዱስትሪዎች ለተኪና ወጪ ንግድ የሚውሉ ምርቶችን በዓይነትና በብዛት የማምረት ስራ ትኩረት ተሰጥቶት መከናወኑን የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ።
መንግስት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን ተግባራዊ በማድረግ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ያለውን ችግር በጋራ በመፍታት ዘላቂነት ያለው እድገትና ተወዳዳሪነት እንዲመዘገብ እያደረገ ይገኛል።
በዚህም በርካታ ኢንዱስትሪዎች የመሰረተ ልማትና ሌሎች ችግሮቻቸው እየተፈታ የማምረት አቅማቸው እየጎለበተ ውጤታማ በመሆን ላይ ናቸው።
ኢንዱስትሪዎች ወጪ ምርቶችን እንዲሁም ተኪ ምርቶችን በራስ አቅም በማምረት የውጭ ምንዛሬ እጥረትን በማቃለል ለሀገር እድገት ያላቸው አስተዋጽኦ እየጨመረ የመጣበት ሁኔታ እየተፈጠረ ይገኛል ።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ የአማራ ክልል ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ እንድሪስ አብዱ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅንቄ በመታገዝ የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም እንዲጎለብት ተደርጓል።
በወራቶቹ በንቅናቄው በተደረገ ጥረት 137 ከፍተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች የውሃ፣ የመብራትና የመንገድ መሰረተ ልማቶች ተሟልተውላቸው ወደ ማምረት ሥራ ተሸጋግረዋል።
በአምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪና የኤክስፖርት ምርቶችን በዓይነትና በብዛት በማምረት ለሀገር እድገት ጥቅም ላይ ለማዋል ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በዚህም ከ554 ሺህ ቶን በላይ ተኪ ምርት በማምረት መንግስት ሊያወጣ የነበረውን 650 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማዳን ተችሏል ብለዋል።
እንዲሁም በአምራች ኢንዱስትሪዎች የተመረተ 123 ሺህ ቶን ምርት ለውጭ ገበያ መቅረቡን ጠቅሰዋል።
በተጨማሪም ከ306 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ከ2ሺህ 925 በላይ የውጭና የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች ፈቃድ ወስደው ወደ ተግባር እንዲገቡ ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
ፈቃድ የወሰዱ ባለሃብቶች ሙሉ በሙሉ ወደ ማምረት ሲሸጋገሩ ከ450 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩም አመላክተዋል።
በተቋሙ ዲጂታል ቴክኖሎጂን በመተግበር የአገልግሎት አሰጣጡን ግልጽ፣ ፍትሃዊ፣ ምቹና ተጠያቂነት ያለው ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
በቀጣይም ቢሮው አምራች ኢንዱስትሪዎችን በልዩ ሁኔታ በመደገፍ ፈጥነው ወደ ማምረት ሥራ እንዲሸጋገሩና ወደምርት የገቡትም ምርታቸውን እንዲያሳድጉ ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ አመላክተዋል።