በዞኑ ነዳጅን በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተጠቃሚዎች በፍትሃዊነት እንዲያገኙ እየተደረገ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በዞኑ ነዳጅን በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተጠቃሚዎች በፍትሃዊነት እንዲያገኙ እየተደረገ ነው
ሆሳዕና ፡- ሚያዝያ 2/2018(ኢዜአ)፡- በሀዲያ ዞን የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተግባራዊ በመደረጉ ተጠቃሚዎች ፍትሃዊ አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻሉን የዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ገለፀ፡፡
የመካከለኛው ምስራቅ ወቅታዊ ሁኔታን ተከትሎ የነዳጅ አቅርቦት ጫናን ለመቋቋም መንግስት ነዳጅን በቁጠባ ለመጠቀም የሚያስችል የመፍትሔ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፡፡
የመምሪያው ኃላፊ አቶ ተከተል ዶባሞ ለኢዜአ እንደገለጹት ወቅታዊ ችግር የሆነውን የነዳጅ አቅርቦት ችግርን ለመከላከል በመንግሥት የተለያዩ አቅጣጫዎች ተቀምጦ እየተተገበረ ይገኛል፡፡
በነዳጅ አቅርቦት ውስንነት ምክንያት ማህበረሰቡ የሚያገኘው አገልግሎት እንዳይቋረጥ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱን ከህገ ወጥነት ለመከላከልና በቁጠባ ላይ የተመሰረተ ስርጭት ለማከናወን የሚያስችል ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ወደ ተግባር ገብቷል ነው ያሉት፡፡
በዞኑ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተግባራዊ በመደረጉ ተጠቃሚዎች ፍትሃዊ አገልግሎት እንዲያገኙ አስችሏል ብለዋል፡፡
በሀዲያ ዞን ሌሞ ወረዳ የኖክ 3 የነዳጅ ማደያ አስተባባሪ አቶ መሰረት ምትኩ በበከላቸው ማደያው የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱን ለማመጣጠን በመንግሥት በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡
በማደያው የሚገባውን የነዳጅ ምርት ቅድሚያ የሚሰጠውን በማስቀደም ለታለመለት ዓላማ እንዲውል በተገቢው እየሰሩ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡
አለም አቀፋዊ ችግር የሆነውን የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን ከብክነት በፀዳ መልኩ መተግበር እንዳለበት የተቀመጠውን አቅጣጫ በመከተል የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት በመወጣት ላይ እንደሚገኙም ነው የገለጹት፡፡
"በሚሰጣቸው የስምሪት ርቀት መሰረት ለነዳጅ መቅጃ የሚሆን ኩፖን እንደሚሰጣቸውና በዚህም ተገቢ የሆነ አገልግሎት እያገኙ " ስለመሆኑ የተናገረው በህዝብ ማመላሻ ትራንስፖርት ማሽከርከር ላይ የተሰማራው ማሙሽ አበበ ነው፡፡
ይህም ለማህበረሰቡ የሚሰጡትን የትራንስፖርት አገልግሎት በተገቢው እንዲያቀላጠፉ ማገዙንም ነው የገለፀው፡፡
በከተማው የትራንስፖርት አገልግሎት ሲሰጡ ያገኘናቸው አቶ ጌታሁን ጸጋዬ እንደገለፁት የነዳጅ አቅርቦት እጥረት ቢኖርም ያለውን በተገቢው እንዲጠቀሙና ማህበረሰቡን እንዲያገለግሉ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡
የሚያገኙትን ነዳጅ በተገቢው ቆጥበው እንዲጠቀሙ የተቀመጠውን ሀገራዊ አቅጣጫ ተግባራዊ ማድረጉ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ስለመሆኑ ጠቁመዋል።
ያጋጠመውን ችግር ከግምት በማስገባት ማህበረሰቡን በተገቢው ለማገልገል እንዲቻል እየተደረገ ያለው ጥረት መጠናከር እንዳለበትም ነው የገለጹት፡፡