በሃዋሳ ከተማ የትንሳኤ በዓል ገበያ በቂ የምርት አቅርቦት የታየበትና ዋጋውም የተረጋጋ ነው - ሸማቾችና ሻጮች - ኢዜአ አማርኛ
በሃዋሳ ከተማ የትንሳኤ በዓል ገበያ በቂ የምርት አቅርቦት የታየበትና ዋጋውም የተረጋጋ ነው - ሸማቾችና ሻጮች
ሀዋሳ፤ ሚያዚያ 2/2018 (ኢዜአ)፡-በሃዋሳ ከተማ የትንሳኤ በዓል ገበያ በቂ የምርት አቅርቦት የታየበትና ዋጋውም የተረጋጋ መሆኑን ሸማቾችና ሻጮች ገለጹ።
የሃዋሳ ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ በበኩሉ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ጨምሮ በ7 የገበያ ማዕከላት ለበዓሉ የሚሆኑ ምርቶች በስፋት መቅረባቸውን ተናግሯል፡፡
መጪውን የትንሳኤ በዓል ምክንያት በማድረግ በሃዋሳ በተለያዩ የገበያ ማዕከላት ኢዜአ በመዘዋወር የበዓል ግብይትን ተመልክቷል፡፡
በዚህ ወቅት አስተያየታቸውን የሰጡ ሸማቾችና ሻጮች በበዓል ገበያ በቂ የምርት አቅርቦት የታየበትና ዋጋውም የተረጋጋ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አቶ ገመቹ ገሹራ እና ወይዘሮ እርጎ ጫካ የተባሉ የሃዋሳ ከተማ ነዋሪ በከተማ አስተዳደሩ ለበዓሉ የተከፈቱ የገበያ ማዕከላት ከሌሎች ገበያዎች ምርቶችን በቅናሽ ማቅረባቸው ገበያውን እያረጋጋው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ለበዓሉ ሽንኩርት፣ እንቁላል፣ ዱቁትና ሌሎች ለበዓል የሚሆኑ የፍጆታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ እየተሸጡ መሆኑንና የምርት አቅርቦትም የተሻለ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
መንግስት በዓሉን ምክንያት በማድረግ የዋጋ ጭማሪና የምርት እጥረት እንዳይኖር የተለያዩ የግብይት ማዕከላትን ማደራጀቱ በተለይ የአቅመ ደካሞችና የመንግስት ሠራተኛውን ችግር ይቀርፋል ብለዋል፡፡
ከተማ አስተዳደሩ ገበያን ለማረጋጋት የጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል፡፡
የመላ ሁለገብ ሃላፊነቱ የተወሰነ መሰረታዊ ህብረት ሥራ ማህበር ሰብሳቢ አቶ ኢዮብ አለሙ በበኩላቸው ማህበሩ ለበዓል የሚሆኑ ምርቶችን ለሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ገበያ የማረጋጋት ሥራ እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን ከሌሎች ገበያዎች በተወሰነ ቅናሽ እያቀረቡ መሆኑን ጠቁመው፣ የክልሉ መንግስትና ከተማ አስተዳደሩ ባደረጉላቸው ድጋፍ ከተለያዩ አካባቢዎች ምርቶችን ማስገባታቸውን ተናግረዋል፡፡
በዚህም ምርቶችን በበቂ ሁኔታ በማቅረብ የተረጋጋ የበዓል ገበያ እንዲኖር ማስቻሉን ገልጸዋል።
የሃዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ አገና ኔቶ በበኩላቸው ለትንሳኤ በዓል ገበያ ምርቶችን በበቂ ሁኔታ በማቅረብ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር ለማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ከክልሉና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ ነው ብለዋል፡፡
ለዚህም በሕብረት ሥራ ማህበራት፣ በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች እንዲሁም በአምራቾች አማካኝነት የግብርና፣ የኢንዱስትሪና ሌሎች የፍጆታ ምርቶችን በማቅረብ ሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲሸምት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
በዚህም የበዓል ገበያ ከማረጋጋት ባለፈ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት የግብይት ሰንሰለቱን ለማሳጠር መሰራቱን ነው የገለጹት።
ወቅታዊ ሁኔታው በህብረተሰቡ ላይ ጫና እንዳያሳድር በ7 የግብይት ማዕከላት የተለያዩ የእርድ እንስሳት እንዲሁም በ36 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች አማካይነት ደግሞ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች እየቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ሰሞኑን ካጋጠመ የነዳጅ እጥረት ጋር ተያይዞ በምርቶች ላይ ያልተገባ ዋጋ የሚጨምሩ ህገ ወጥ ነጋዴዎችን ለመቆጣጠርም ግብረ ሃይል ተቋቁሞ ክትትልና ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሃላፊው አክለው የተለያዩ የገበያ አማራጮችን በማመቻቸት ገበያውን ለማረጋጋት የተጀመረው ሥራ ውጤታማ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡