በባህር ዳር ከተማ የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ የማዕድ ማጋራት መርሃ ግብር ተከናወነ - ኢዜአ አማርኛ
በባህር ዳር ከተማ የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ የማዕድ ማጋራት መርሃ ግብር ተከናወነ
ባህርዳር ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በባህር ዳር ከተማ የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ ለ300 አቅመ ደካማ ወገኖች የማዕድ ማጋራት መርሃ ግብር ተከናወነ።
የባህር ዳር ከተማ የበጎ አድራጎት ማህበር በከተማዋ ለሚገኙ 300 አቅመ ደካማ ወገኖች የትንሳኤ በዓልን ምክንያት ያደረገ ማዕድ አጋርቷል።
የማህበሩ ስራ አስኪያጅ አቶ አህመድ ይማም ማዕድ ባጋሩበት ወቅት እንደገለፁት ማህበሩ በዓል ሲመጣ ለአቅመ ደካማ ወገኖች የበዓል መዋያ ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል።
ዛሬም የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ በባህርዳር ከተማ በሶስት ክፍለ ከተሞች ለሚገኙ 300 አቅመ ደካማ ወገኖች የገንዘብና የዶሮ ድጋፍ ማድረጉን ገልፀዋል።
እንዲሁም በፋና የበጎ አድራጎት ማህበር ለታቀፉ አቅመ ደካማ ወገኖች አንድ የበሬ ሰንጋ ለበዓል መዋያ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቀዋል።
የፋሲሎ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ገረመው አባተ በበኩላቸው፤ በጎ አድራጎት ማህበሩ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ አቅመ ደካማ ወገኖች እያደረገ ላለው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።
ማህበሩ ከ3 ሺህ 300 በላይ ለሚሆኑ አቅመ ደካማ ወገኖች በየዓመቱ የጤና መድህን ወጪን በመሸፈን ጤናቸውን እንዲጠብቁ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ተመልክቷል።
የጣና ክፍለ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ የሺኢትዮጵያ መኮነን የተደረገው ድጋፍ በዓሉን ከቤተሰባቸው ጋር ተደስተው እንዲያሳልፉ ምክንያት ይሆናል ብለዋል።
የፋሲሎ ክፍለ ከተማ ነዋሪ እማሆይ ማንአህሎሽ ደርሶ በበኩላቸው፤ በጎ አድራጎት ማህበሩ በዓል በመጣ ቁጥር የዶሮና የዘይት ድጋፍ ስለሚያደርግልን በዓሉን ሳንቸገር እንድናሳልፍ ረድቶናል ብለዋል።
በተጨማሪም በየዓመቱ የጤና መድህን ወጪያቸውን በመሸፈን ጤንነታቸውን እንዲጠብቁ እያገዛቸው እንደሚገኝም ገልጸዋል።