የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት በትኩረት እየተሰራ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት በትኩረት እየተሰራ ነው
ደብረ ማርቆስና ገንዳውኃ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃምና በምዕራብ ጎንደር ዞኖች የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን የዞኖቹ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያዎች ገለጹ።
በዞኖቹ መጪውን የትንሳኤ በዓል አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት ለሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ብድር ከማመቻቸት አንስቶ ጊዜያዊ የገበያ ቦታዎች እስከ ማዘጋጀት የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውም ተመላክቷል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ተወካይ ሃላፊ አቶ መለሰ የተመኝ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት በትኩረት እየተሰራ ነው።
ለሸማቶች ህብረት ስራ ማህበራት ከ24 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር በመመደብና ለአቅራቢ ኢንተርፕራይዞች ጊዜያዊ የገበያ ማዕከላትን በማቋቋም ምርት በስፋትና በዓይነት እንዲቀርብ ተደርጓል ብለዋል።
በዚህም ከ94 ሺህ ሊትር በላይ ዘይት፣ 877 ኩንታል የዳቦ ዱቄት፣ ከ1 ሺህ 800 ኩንታል በላይ ስኳር፣ ሽንኩርትና ሌሎች ለበዓል ገበያ የሚያስፈልጉ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ መቻሉን ተናግረዋል።
በተጨማሪም ከ18 ሚሊዮን ሊትር በላይ ወተት፣ ከ277 ሺህ በላይ ዶሮ፣ ከአንድ ሚሊዮን በላይ እንቁላል እንዲሁም ከ50 ሺህ በላይ የደለቡ በሬዎች፣ በጎችና ፍየሎች መቅረባቸውን አስረድተዋል።
በዞኑ የአነደድ ወረዳ የአንበር ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ትግስት መላኩ እንደገለጹት፤ ገበያውን ለማረጋጋት የተደረገው ጥረት ህብረተሰቡ በአቅሙ ልክ የሚያስፈልገውን ገዝቶ ተደስቶ እንዲውል የሚያደርግ ነው።
በዞኑ በማቻከል ወረዳ የአማኑኤል ከተማ ነዋሪ አቶ ይሁን አዲስ በበኩላቸው፤ ስኳርና እንቁላልን በመደበኛ ገበያ ካለው በቅናሽ ዋጋ እየገዙ መሆኑን ተናግረዋል።
በተያያዘ ዜና ምዕራብ ጎንደር ዞን የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ ተወካይ አቶ መብራቱ አዲስ እንደገለጹት፤ በዓሉን አስመልክቶ የአቅርቦት እጥረትና ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር ከባለድርሻ አካላት ጋር እየተሰራ ነው።
በተሰራው ስራም የእርድ እንስሳት፣ ዘይት፣ ስኳር፣ የዳቦ ዱቄትና ሌሎች መሰረታዊ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በበቂ ሁኔታ ማቅረብ መቻሉን አረጋግጠዋል።
በዞኑ ከ200 ሺህ በላይ ሰንጋ፣ ፍየልና በግ ለበዓሉ የቀረበ መሆኑን ጠቁመው ግብረ ሃይል በማቋቋም ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉና ምርት በሚደብቁ ህገወጦች ላይ ርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ጠቁመዋል።
በገንዳውሃ ከተማ ሲገበያዩ ያገኘናቸው አቶ ገብረማርያም አዱኛ በሰጡት አስተያየት የእርድ እንስሳት እንቁላልና አንዳንድ ለበዓል የሚያስፈልጉ ምርቶች አቅርቦት ካለፉት ዓመታት የተሻለ ነው ብለዋል።
ይህም ህብረተሰቡ በአቅሙ የሚፈልገውን ገዝቶ በዓሉን በደስታ ለማሳለፍ የሚያስችል ነው ብለዋል።