ቀጥታ፡

ጅቡቲ ለኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ጭነቶች ቅድሚያ የመስጠት ተግባሯን ትቀጥላለች

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ ጅቡቲ ወደ ኢትዮጵያ ለሚጓጓዙ ጭነቶች ቅድሚያ መስጠቷን አጠናክራ እንደምትቀጥል የጅቡቲ ወደቦችና ነፃ የንግድ ቀጣና ባለስልጣን (DPFZA) ሰብሳቢ አቡበከር ዑመር ሃዲ ገለጹ።

የጅቡቲ ወደቦችና ነፃ የንግድ ቀጣና ባለስልጣን (DPFZA) ሰብሳቢ አቡበከር ዑመር ሃዲ የጅቡቲ ባህር ወደቦች በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ የመጣውን የጭነት መጠን ያለምንም መጨናነቅ ማስተናገድ የሚችል አስተማማኝ አቅም እንዳላቸው ለኢዜአ ገልጸዋል።

ወደ ወደብ የሚመጡ ማናቸውም የኢትዮጵያ ጭነቶች በተለይም ማዳበሪያ ሳይዘገዩ ወደ መሐል ሀገር እንዲጓጓዙ ቅድሚያ እየተሰጣቸው መሆኑን ተናግረዋል።

ላለፉት በርካታ ዓመታት ጅቡቲ ከ90 በመቶ በላይ የሚሆነውን የኢትዮጵያን የገቢና ወጪ ንግድ እያስተናገደች ትገኛለች።

ይህ ታሪካዊ ትስስር የሁለቱ ሀገራት ወንድማማችነት ይበልጥ እንዲጠናከር ምክንያት ሆኗል።

የሁለቱን ሀገራት የንግድ ትስስር በማቀላጠፍ ረገድ ዘመናዊውና በኤሌክትሪክ የሚሰራው የአዲስ አበባ-ጅቡቲ የምድር ባቡር ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል።

ይህ ስትራቴጂካዊ የትራንስፖርት ኮሪደር የሎጂስቲክስ ቅልጥፍናን በማሻሻል የትራንዚት ጊዜን በእጅጉ መቀነስ ያስቻለ ሲሆን፣ የንግድ እንቅስቃሴውን ፈጣንና ውጤታማ አድርጎታል።

በኢትዮጵያ እየታየ ያለው የኢንዱስትሪ መስፋፋት፣ የመሠረተ ልማት ግንባታና የንግድ ዕድገት ለወደብ አገልግሎት ፍላጎት ማደግ ምክንያት ሆኗል።

በወደብ ስራዎች ላይ አልፎ አልፎ የሚታዩ የመርከቦች የአንድ ወይም የሁለት ቀናት መዘግየቶች ከዓለም አቀፍ አሰራር አንጻር የተለመዱ መሆናቸውንም አንስተዋል።

ሀገራቱ ያላቸውን ጠንካራ የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ ለማገዝ፣ ጅቡቲ በአንዳንድ የወደብ ሀብቶች ላይ ኢትዮጵያ የባለቤትነት ድርሻ (አክሲዮን) እንዲኖራት ሃሳብ ማቅረቧን ጠቁመዋል።

ይህ አዲስ አቀራረብ የሁለቱን ሀገራት ኢኮኖሚያዊ ትስስር ወደ ላቀ የባለቤትነት ደረጃ የሚያሸጋግርና ለዘላቂ ጥቅማቸው ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል።

በየብስ ትራንስፖርት በተለይም በባቡርና በመኪና መንገድ ላይ የሚታዩ ጫናዎችን ለማቃለል ጅቡቲ አዳዲስ ስልቶችን እየቀረጸች መሆኑም ታውቋል።

ከመርከብ ወደ መርከብ የሚደረጉ የጭነት ማስተላለፍ (Transshipment) ስራዎችን በማስፋፋትና ተጨማሪ የማከማቻ መጋዘኖችን በመገንባት የሎጂስቲክስ ዘርፉን ይበልጥ ዘመናዊ ለማድረግ ታቅዷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም