ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ እ.ኤ.አ በ2040 ዓመታዊ ገቢውን 30 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ አቅዷል

አዲስ አበባ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ እ.ኤ.አ በ2040 ዓመታዊ ገቢውን 30 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ማቀዱን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለፁ።

አየር መንገዱ ፈተናዎችን በጽናት በማለፍ አፍሪካን ከዓለም ጋር የሚያገናኝ ቀዳሚ የአቪዬሽን ተቋም መሆኑን በተግባር ማረጋገጡንም ጠቅሰዋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ 80ኛ ዓመት የምስረታ በዓልን አስመልክቶ የአየር መንገዱ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። 

ዋና ስራ አስፈፃሚው፤ ተቋሙ ባለፋት ስምንት አስርት ዓመታት የኢትዮጵያ የዕድገት፣ የትርፋማነት እና የሀገር ኩራት ምሳሌ ሆኖ መዝለቁን ገልጸዋል።

አየር መንገዱ የመጀመሪያ በረራውን  መጋቢት 30 ቀን 1938 ዓ.ም ማድረጉን ያስታወሱት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ በነበሩት ዓመታት ባስመዘገበው ተከታታይ ዕድገት በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ 145 መዳረሻዎች ያሉት ግዙፍ አየር መንገድ ለመሆን መብቃቱን ተናግረዋል።

ተቋሙ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን ተወዳዳሪነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር ራዕይ 2040 የተሰኘ ስትራቴጂክ እቅድ ማዘጋጀቱን አስታውቀዋል።

ይህ እቅድ አየር መንገዱ በሚቀጥሉት ዓመታት የበረራ አድማሱን፣ የንብረት አቅሙን እና የገቢ መጠኑን በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ የሚያስችለው ነው ብለዋል።

በዚህም መሰረት አየር መንገዱ በአሁኑ ወቅት ያሉትን 145 ዓለም አቀፍ መዳረሻዎችን ወደ 243 ለማድረስ ማቀዱን ገልጸዋል።

በአሁኑ ወቅት አገልግሎት እየሰጡ ያሉትን 150 አውሮፕላኖች ከእጥፍ በላይ በማሳደግ ቁጥራቸውን 350 ለማድረስ ታቅዷል ነው ያሉት።

ዓመታዊ  መንገደኞችን የማጓጓዝ አቅሙን አሁን ካለበት 20 ሚሊዮን ወደ 60 ሚሊዮን ከፍ ለማድረግ  ግብ መቀመጡንም ተናግረዋል።

በአሁኑ ወቅት በዓመት የሚጓጓዘውን 850 ሺህ ቶን የጭነት መጠን ወደ 2 ነጥብ 1 ሚሊዮን ቶን ለማሳደግ ታቅዷል ነው ያሉት።

አየር መንገዱ በስትራቴጂክ እቅዱ ዓመታዊ ገቢውን 30 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ግብ መያዙን ዋና ስራ አስፈፃሚው አስታውቀዋል።

የአሁኑ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የታቀደውን ግዙፍ ዕድገት ለማስተናገድ በቂ ባለመሆኑ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፈያ የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል።

ከዓለም አቀፍ በተጨማሪ የሀገር ውስጥ የበረራ መዳረሻዎችን በእጥፍ ለማሳደግ እየሰራ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም