ቀጥታ፡

ምክር ቤቱ የኢትዮጵያን አምራች ኢንዱስትሪ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የነቃ ተሳትፎ ሊያደርግ ይገባል

አዲስ አበባ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሀገር አቀፍ የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት የአምራች ኢንዱስትሪውን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ በትጋት መሥራት እንዳለበት የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ።

የኢትዮጵያ ሀገር አቀፍ የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ባካሄደው 9ኛው ጠቅላላ ጉባኤ፣ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጀማል አህመድን ፕሬዝዳንት አድርጎ መርጧል።

በምክትል ፕሬዝዳንትነት ደግሞ ባለሀብቱ አቶ በላይነህ ክንዴ የተመረጡ ሲሆን፣ ጉባኤው የዳይሬክተሮች ቦርድ አባላት ምርጫንም በስኬት አጠናቋል።


 

በጉባኤው ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል፣ መንግሥት አምራች ኢንዱስትሪው በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ጉልህ ሚና እንዲኖረው ለማስቻል መሰረት የሚጥሉ ተግባራት እያከናወነ ነው ብለዋል።

በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካትና ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ተጨባጭ ለውጥ መጥቷል ነው ያሉት።

መንግሥት ለአምራች ኢንዱስትሪው ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን በማንሳት፥ ይህን ለማስፋት ምክር ቤቱ በሂደቱ ግብዓት የመስጠትና የነቃ ተሳትፎ የማድረግ ኃላፊነት እንዳለበት አስገንዝበዋል።

በአምራች ዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን በተደራጀ መንገድ ለመንግሥት በማቅረብና በፖሊሲ ግብዓቶች ላይ በንቃት በመሳተፍ የዘርፉን ተወዳዳሪነት እንዲያረጋግጥ አጽንኦት ሰጥተዋል።

መንግሥት ለአምራች ዘርፉ ምቹ የሥራ አውድ ለመፍጠር የፖሊሲና የሕግ ማሻሻያዎችን ማድረጉን ጠቅሰው፣ ዘርፉ በወጪ ንግድና በኢኮኖሚ ዕድገት ላይ አወንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ገልጸዋል።

አዲሱ የምክር ቤት አመራር ተኪ ምርትን በማስፋት፣በሥራ ዕድል ፈጠራና ወጪ ንግድ ላይ አምራች ኢንዱስትሪው በላቀ ሁኔታ እንዲሠራ የማድረግ ሃላፊነቱን እንዲወጣ አስገንዝበዋል።


 

አዲሱ የምክር ቤቱ ፕሬዝዳንት አቶ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፣ ምክር ቤቱ ከአምራች ኢንዱስትሪው ጋር ተቀራርቦ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል።

ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው ምርት እንዲኮሩ ግንዛቤ ማስረጽ፣ የኢትዮጵያን የወጪ ንግድ ምርቶች በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ማድረግ፣ ከዘርፉ ጋር የተያያዙ ችግሮችን ከመንግሥት ጋር በመሆን በዘላቂነት መፍታት ላይ በትጋት ይሠራል ነው ያሉት።

የኢትዮጵያ ሀገር አቀፍ የዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት የቀድሞ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አበባየሁ ግርማ፤የምክር ቤቱ አመራሮች ምርጫ ዲሞክራሲያዊነቱን ጠብቆ የተካሄደና ስኬታማ መሆኑን አንስተዋል።


 

ምክር ቤቱ በተለይ በከፍተኛ አምራቾች በአነስትኛ ኢንዱስትሪዎች መካከል የልምድና የቴክኖሎጂ ልውውጥን በማስፋት ረገድ በትኩረት እንዲሠራ ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም