ቀጥታ፡

በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የዲጅታል ልማት ስትራቴጂ ትልቅ ስኬት የተመዘገበበት ነው

መቀሌ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የዲጅታል ልማት ስትራቴጂ ትልቅ ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ተናገሩ።

የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ትግበራ በስኬት መጠናቀቁን ተከትሎ በቀጣይ አምስት ዓመታት የሚከናወን ቀጣይነት ያለው ስትራቴጂክ ፕላን ይፋ በማድረግ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩ ይታወቃል።

የ2025 ስትራቴጂክ ተግበራ ስኬት ተደርገው ከሚወሰዱት መካከል የባንኮች የዲጅታል አገልግሎት መሳለጥ፣ የቴሌብር አገልግሎት፣ የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ፣ የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ስልጠና እና ሌሎችም ይገኙበታል።

የአርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ፤ የአዳዲስ ፈጠራዎች፣ የተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ በዲጅታል የታገዙ መሆናቸውም ለዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ማሳያዎች መሆናቸውን መግለጽ ይቻላል።

ከዚህ ስኬትም በመነሳት የዲጅታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ይፋ ተደርጎ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በመደረግ ላይ ይገኛል።

በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ በትግራይ ክልል ያነጋገራቸው የዘርፉ ባለሙያዎች በዲጅታል ልማት ባለፉት አምስትና ስድስት ዓመታት የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ከባለሙያዎቹ መካከል ሰሎሞን ፀጋይ፤ በተለይም የቴሌብር አገልግሎት፣ የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ፣ የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ስልጠና ለዘርፉ መሰረት ያኖሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።

የተቋማት የዲጅታል አገልግሎት እየተስፋፋ መምጣት ሌላኛው ስኬት መሆኑንም ጠቅሰዋል።

ከዚህ ስኬት በመነሳትም በቀጣይ አምስት አመታት የሚተገበረው ስትራቴጂክ እቅድ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርጋት መሆኑን ገልጸዋል።

የድጅታል ቴክኖሎጂ ምርምርና ጥናት ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት አቶ ሰሎሞን ገብረመድህን በበኩላቸው በተለይም ወጣቶች የኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው ለዘርፉ ልማትና አድገት ትልቅ አቅም መሆኑን ተናግረዋል።

በመሆኑም የዲጅታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ እቅድን ለማሳከት ስልጠናዎች እንዳሉ ሆነው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና የዘርፉ ባለሙያዎች በጥናትና ምርምር የተደገፈ ስራ ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል።

ሌላኛው የቴክኖሎጂ ባለሙያ ሀጎስ ገብረፃድቅ፤ በዲጅታል ቴክኖሎጂ እንደ ሀገር የተከናወኑ ተግባራትና በቀጣይ የተያዙ እቅዶች የሚያጓጉ መሆኑን ገልጸዋል።

በገጠርና በከተሞች የዲጅታል አገልገግሎትን በማስፋት ዜጎች ፈጣን፣ ፍትሃዊና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ መትጋት ይጠበቅብናል ብለዋል።

በአገልግሎት አሰጣጥ ሂደት ሌብነትና ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከልም የዲጅታል ትግበራ የማይተካ ሚና የሚኖረው መሆኑን አስረድተዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም