የኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ተጨባጭ ለውጦች እንዲመዘገቡ አስችሏል - ፕሮፌሰር ስቴፋን ዴርኮን - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ተጨባጭ ለውጦች እንዲመዘገቡ አስችሏል - ፕሮፌሰር ስቴፋን ዴርኮን
አዲስ አበባ፤መጋቢት 29/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ ተጨባጭ ለውጦች እንዲመዘገብ ማስቻሉን የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ስቴፋን ዴርኮን ገለጹ፡፡
የገንዘብ ሚኒስቴር ባለፉት 18 ወራት የተከናወኑ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ እና መዋቅራዊ ማሻሻያዎችን ውጤታማነት የሚገመግም ዝርዝር ሪፖርት ይፋ አድርጓል።
በሪፖርቱ መሠረት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተወሰዱ እርምጃዎች ውጤት እያሳዩ መሆኑን የተጠቀሰ ሲሆን የወጪ ንግድ ገቢ በማሳደግ ረገድ እንዲሁም ሌሎችም ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ተመዝግበዋል።
በዚሁ ወቅት የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ስቴፋን ዴርኮን በበይነ መረብ ባስተላለፉት መልዕክት የኢትዮጵያን ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ አስመልክቶ ንግግር አድርገዋል፡፡
በዚህም የኢትዮጵያ መንግስት ተግባራዊ እያደረገ ያለው የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ መረጋጋትን ከመፍጠር አንጻር ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገቡን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ላለፉት ሦስት አስርት ዓመታት በቅርበት ሲከታተሉ እንደቆዩ አስታውሰው፣ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ከፍተኛ ዕድገት ማስመዝገቧን ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ በርካታ ለውጦችን ማስመዝቡን ጠቅሰው የውጭ ምንዛሬ ተመን ማሻሻያ በተሳካ ሁኔታ መከናወኑ፣ የዋጋ ግሽበት መቀነስ ማሳየቱ እና የሀገሪቱ የውጭ ምንዛሬ ክምችት መሻሻሉ ይበል የሚያሰኝ ነው ብለዋል፡፡
በተጨማሪም የወጪ ንግድ ከፍተኛ እምረታ ማሳየት መጀመሩ እንዲሁም ፋይናንስ የተረጋጋ መሆኑን አድንቀዋል፡፡
ሪፖርቱ በውጭ አማካሪዎች ሳይሆን በገንዘብ ሚኒስቴር ውስጥ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች መዘጋጀቱን አድንቀው የፖሊሲ ማሻሻያዎች ስኬታማ የሚሆኑት በሀገር በቀል ተንታኞች ተቀርጸውና በባለቤትነት ሲመሩ የሪፖርቱን ተዓማኒነት ከፍ ያደርገዋል ብለዋል።
ማንኛውም የኢኮኖሚ ፖሊሲ ውጤታማ ሊሆን የሚችለው የሀገሪቱን ተጨባጭ ኢኮኖሚያዊ፣ ተቋማዊና ፖለቲካዊ አውዶች በጥልቀት ከግምት ውስጥ ሲያስገባ መሆኑን አክለው ገልጸዋል።
ስኬታማ የተሟላ የኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀገር ውስጥ የትንታኔ አቅም ላይ በእጅጉ የተመሰረተ መሆኑን በማድነቅ የኢትዮጵያ ባለሙያዎች ለሪፖርቱ መሳካትና ለፖሊሲዎቹ መቃናት ያበረከቱትን አስተዋጽኦ አድንቀዋል።
ሪፖርቱ በመረጃ ላይ የተመሰረተ ግልጽ ውይይት እንዲኖር እና ለወደፊት የፖሊሲ እርምጃዎች እንደ መነሻ የሚያገለግል መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡