ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነት ስኬት የተኪ ምርት አቅምን እና የወጪ ንግድ ተወዳዳሪነትን እያሳደገ ነው

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነት ስኬት የተኪ ምርት አቅምን በማጎልበት የወጪ ንግድ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን እያሳደገ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገለጸ።

በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ተቀርፀው ወደ ተግባር የተቀየሩ የብዝሃ-ኢኮኖሚ ስትራቴጂዎች ዛሬ ላይ በግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና ቴክኖሎጂ ዘርፎች ተጨባጭ ውጤት አስገኝተዋል።


 

የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያም የኢንዱስትሪ ዘርፍ መዋቅራዊ የድጋፍና ክትትል ሥርዓት በማጎልበት በወጪ ንግድና ተኪ ምርት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን እያረጋገጠ ነው።

በኢንዱስትሪ ዘርፍ የተመዘገበው እመርታም በኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ ድርሻ የሚያበረክትበትን ወሳኝ ዕድል በመፍጠር እያገለገለ ይገኛል።

የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡልልታ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የኢንዱስትሪ ምርታማነትን የሚያበረታታ አስቻይ የፖሊሲ እርምጃ ተወስዷል።


 

የኢንዱስትሪ ዘርፍ ስትራቴጂክ የፖሊሲ እረምጃው የአምራቾችን የመሠረተ ልማት፣ የኃይልና የፋይናንስ አቅርቦት ማነቆዎችን በቅንጅታዊ የአሰራር ሥርዓት መፍትሔ መስጠት እንዳስቻለ ተናግረዋል።

በተጨማሪም የሀገር ውስጥና የውጭ የኢንዱስትሪ ዘርፍ የኢንቨስትመንት አልሚዎችን ፍሰት በማሳደግ በሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ገንቢ ሚና የሚወጣበትን ወሳኝ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ታምርት ሀገር አቀፍ ንቅናቄም ዝቅተኛ የኢንዱስትሪ የማምረት ታሪክ በመቀየር በዘርፉ ላይ እመርታዊ መነቃቃት መፍጠሩን አንስተዋል።

ይህም ኢትዮጵያን የዓለም አቀፍ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት የስበት ማዕከል እንድትሆን እያደረጋት ነው ብለዋል።


 

የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያም ሌላኛው ለአምራች ኢንዱስትሪ ምርታማነት አቅም የፈጠረ ወሳኝ ዕድል መሆኑን ገልጸዋል።

ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እሳቤውም የኢንዱስትሪ ምርታማነትን በማሳለጥ አስቻይ የተኪና ወጪ ንግድ አቅም እንዲፈጠር ማድረጉን አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ የመጀመሪያ ካፒታል ገበያ ሥርዓት ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ከፍተኛ ፋይዳ እያበረከተ መሆኑን አብራርተዋል።

የካፒታል ገበያም የአምራች ኢንዱስትሪ የፋይናን አቅርቦት ፍላጎትን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አማራጭና የረጅም ጊዜ ቁጠባን የሚያበረታታ አስቻይ የአሰራር ምኅዳር እንደፈጠረ አንስተዋል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም