ቀጥታ፡

በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል

አምቦ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባለፉት የለውጥ ዓመታት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል ሲሉ የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አወሉ አብዲ ተናገሩ።

ለውጡን ምክንያት በማድረግ በምዕራብ ሸዋ ዞንና በአምቦ ከተማ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተሳተፉበት የድጋፍ ሰልፍ ተካሂዷል።


 

በህዝባዊ ሰልፉ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት አቶ አወሉ አብዲ፤ በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል ብለዋል።

በእነዚህ ዓመታት በየአካባቢው ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ በተለይም በኢኮኖሚው ዘርፍ ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል።

በግብርናው ዘርፍ ከባህላዊ የአስተራረስ ዘዴ በመውጣትና በሜካናይዜሽን በመታገዝ ራስን በምግብ ከመቻል ባለፈ ምርትን ለውጭ ገበያ ማቅረብ ተችሏል ነው ያሉት።

በከተማ ልማትም ከተማዎችን በቴክኖሎጂ ከማዘመን ባለፈ የ"አንድ ማዕከል" አገልግሎት በማስጀመር ህዝቡ ቀልጣፋና ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኝ ተደርጓል ብለዋል።

በለውጡ ዓመታት የተመዘገቡ የልማት ስኬቶችን ለማስቀጠል ዘላቂ ሰላምን በማረጋገጥ ህዝቡ በአንድነት ሊቆም እንደሚገባ አሳስበዋል።


 

የምዕራብ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ በበኩላቸው፤ የለውጡ መንግስት ቀደም ሲል የነበሩ ውስብስብ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ችግሮችን በመፍታት ትላልቅ ፕሮጀክቶችን ማከናወኑን ገልጸዋል።

ዘንድሮም በ6ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለህዝብ የገባነውን ቃል አክብረን፣ ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ አዲስ ቃልኪዳን የምንገባበትና የተጀመሩ ልማቶችን የምናስቀጥልበት ነው ብለዋል።


 

የአምቦ ከተማ ከንቲባ አቶ ሃጫሉ ገመቹ፤ በከተማው ከመጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም በኋላ በሁሉም የልማት ዘርፎች የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል።

በድጋፍ ሰልፉ ላይ የተሳተፉ ነዋሪዎችም በለውጡ ዓመታት በተመዘገቡ የልማት ስራዎች ተሳታፊ እና ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።

ወጣት ዳግማዊት ቁምላቸው፤ የተገኙ ስኬቶችን በመጠበቅና የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ የሀገሪቱን እድገት ለማፋጠን ዝግጁ መሆኗን ገልጻለች።


 

ሌሎች ወጣቶችም ለሀገራቸው እድገት በጋራ እንዲሰሩ ጥሪ አቅርባለች።


 

አቶ ንጉሴ ጆሮ በበኩላቸው፤ ህብረተሰቡ በአንድነት በመቆም ለሰላምና ለልማት አስተዋጽኦውን ማስቀጠል ይጠበቅበታል ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም