ቀጥታ፡

በለውጡ መንግስት በተከናወኑ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ ሆነናል -ነዋሪዎች

ነቀምቴ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦በለውጡ መንግስት በተከናወኑ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን የነቀምቴ፣ የመቱ እና የጭሮ ከተሞች ነዋሪዎች ተናገሩ።   

የምስራቅ ወለጋ ዞን፣ የኢሉአባቦር ዞን እና የምዕራብ ሀረርጌ ዞን ነዋሪዎች የለውጡ መንግስት የተመሰረተበትን 8ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ፣ በነቀምቴ፣ በመቱ እና በጭሮ ከተሞች የድጋፍ ሰልፎችን አካሂደዋል። 

ሰልፈኞቹ ላለፉት ስምንት ዓመታት የተመዘገቡ ስኬቶችን በመደገፍ እና የሰላም ጥሪዎችን በማስተጋባት ድምጻቸውን አሰምተዋል።   


 

በነቀምቴ በተካሄደው ሰልፍ ላይ የተሳተፉት የከተማው 07 ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ማረሜ ተፈራ፣ በለውጡ መንግስት በተከናወኑ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። 

በተለይም በነቀምቴ ከተማ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ስራ ከተማዋን ለኑሮ ምቹ ከማድረግ ባለፈ ገጽታዋን በተሻለ መልኩ የለወጠ መሆኑን ጠቅሰዋል። 

በእነዚህ የለውጥ ዓመታት የተመዘገቡ ውጤቶችን ለማስቀጠል ከመንግስት ጎን ተሰልፈው የሚጠበቅባቸውን እንደሚወጡ አስረድተዋል።   

የሰልፉ ታዳሚዎች አቶ ጌታቸው ታደገ እና ወይዘሮ ጫልቱ ጥላሁን በለውጡ ዓመታት የተከናወኑ ስራዎች ተጠቃሚነታቸውን ያሳደጉ መሆናቸውን ይናገራሉ። 

በአካባቢው የተጀመሩ ትላልቅ የልማት ስራዎች ቀጣይነት እንዲኖራቸው ሰላምን የማጽናት ስራ ላይ በንቃት እንደሚሳተፉ ገልጸዋል።   

በተመሳሳይም በኢሉአባቦር ዞን መቱ በተካሄደው የድጋፍ ሰልፍ ላይም የዞኑ ነዋሪዎች አዳዲስ የግብርና ልማት ስራዎችን አጠናክረን በማስቀጠል ለሁለንተናዊ ተጠቃሚነታችንና ለሀገር እድገት መረጋገጥ ጠንክረን እንሰራለን ብለዋል። 


 

በተለይ በዞኑ በግብርና መስክ የተጀመሩ የሩዝ፣ የስንዴ፣ የማር እና የሻይ ልማት ፕሮግራሞች ከለውጡ ወዲህ የተለየ ትኩረት አግኝተው እየተተገበሩ መሆናቸውንም ገልጸዋል። 


 

ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ተስፋዬ ጸጋዬ እና አቶ ተካ መሐመድ፤ ተጠቃሚ ያደረጓቸው የግብርና ልማት ኢኒሼቲቮች የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።   

በጭሮ ከተማ በተካሄደ የድጋፍ ሰልፍ ላይ የተሳተፉት አቶ ኢብራሂም ሁሴን እና ወይዘሮ ነጂማ ሁሴን፤ ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ የረጅም ጊዜ ጥያቄዎቻቸው ምላሽ በማግኘት በመልካም አስተዳደር እና በኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው ማደጉን ገልጸዋል።   


 

የምስራቅ ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ወጋሪ ነገራ በነቀምቴው ሰልፍ ላይ ባደረጉት ንግግር፣ መጋቢት 24 የአንድነትና የወንድማማችነት አዲስ ተስፋ የተሰነቀበት ቀን መሆኑን ገልጸዋል። 

ከለውጡ ወዲህ በዞኑ የተከናወኑ ተግባራት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ ያስቻሉ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ በቀጣይም የተጀመሩ በጎ ተግባራት እንዲቀጥሉ ህዝቡን በማሳተፍ ይከናወናሉ ብለዋል። 

የፊታችን ግንቦት የሚካሄደውን ጠቅላላ ምርጫ ስኬታማ፣ ፍትሃዊና ዲሞክራሲያዊ ለማድረግ ህዝቡ ሰላሙን መጠበቅ እንዳለበትም አሳስበዋል።   

የነቀምቴ ከተማ ከንቲባ አቶ መሰረት ሃይሉ በበኩላቸው፣ የለውጡ መንግስት ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስራዎችን በመስራት ልዩነቶችን ወደ እድል መቀየር መቻሉን ገልጸዋል። 


 

በመቱ ከተማ በተካሄደው ህዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የኦሮሚያ ክልል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ሻፊ ሁሴን፣ መጋቢት 24 የእውነተኛ ህብረ-ብሔራዊነት መሰረት የተጣለበት ነው ሲሉ ገልጸዋል።   


 

ከለውጡ ወዲህ የዞኑን ህዝብ ህይወት በመሰረታዊነት ያሻሻሉ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል ያሉት ደግሞ የኢሉባቦር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ ናቸው። 


 

የምዕራብ ሐረርጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ኢክራም ጠሀ በበኩላቸው፣ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የተመዘገቡ ዘርፈ ብዙ ውጤቶችን በማስቀጠል ረገድ ህብረተሰቡ ይበልጥ ሊረባረብ ይገባል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም