ቀጥታ፡

ኢትዮ ቴሌኮም ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመተባበር አገልግሎቶችን ይበልጥ የሚያዘምን ቴሌሳይን (teleSign) የተሰኘ ዲጂታል ሶሉሽን አስጀመረ

አዲስ አበባ፤መጋቢት 22/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮ ቴሌኮም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ከፍትህ ሚኒስቴር እና ከፌደራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ጋር በመተባበር የመንግስት አገልግሎቶችን ለማዘመን ያለመ ቴሌሳይን (teleSign) የተሰኘ የዲጂታል ሶሉሽን አስጀምሯል።

በማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬሕወት ታምሩ፤ኩባንያው የሀገሪቱን የዲጂታል ሽግግር እውን ለማድረግ የሚያስችሉ ግዙፍ የቴክኖሎጂ መሰረተ-ልማቶችን በስፋት እየዘረጋ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

አዲሱ ቴሌሳይን የተሰኘው ዲጂታል ሶሉሽን በኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን አስረድተዋል።

ይህ አዲስ የቴክኖሎጂ ውጤት አስተማማኝ የዲጂታል ማንነት ማረጋገጫንና ህጋዊ ተቀባይነት ያለውን የዲጂታል ፊርማ ስርዓት ወደ ስራ የሚያስገባ ነው ብለዋል።

ይህም የመንግሥት አሠራሮችን ሙሉ በሙሉ ዲጂታል በማድረግ ረገድ ቁልፍ ሚና ይጫወታል ነው ያሉት።

አሠራሩ በተለይም አሰልቺ ቢሮክራሲን በመቀነስ፣የአገልግሎት ተደራሽነትን በማሳደግ እና ሀገራዊ የዲጂታል ተጠቃሚነትን በማስፈን ረገድ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖረው ዋና ስራ አስፈፃሚዋ ተናግረዋል።

የዲጂታል አገልግሎት መስጫው ዜጎች ያለ ምንም መልክዓ-ምድራዊ ገደብ የመንግስት አገልግሎቶችን በኦንላይን እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ጠቅሰዋል።

ይህም ሀገሪቱ ወደ ሙሉ ዲጂታል መንግሥት (E-Government) የምታደርገውን ሽግግር በእጅጉ የሚያፋጥን ሲሆን፤ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚኖሩ ዜጎች አገልግሎቶችን በፍጥነት፣ በብቃትና በታማኝነት እንዲያገኙ ያስችላቸዋል ብለዋል።

ኢትዮ ቴሌኮም መሰል ዘመናዊ የዲጂታል መፍትሔዎችን በማቅረብ፣ሀገራዊ የዲጂታል ጉዞን የመደገፍና የማብቃት ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አፅንኦት ሰጥተዋል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርሃኑ ፀጋዬ፤ ሚኒስቴሩ የተጣለበትን ተልዕኮ በላቀ ብቃት ለመወጣት የሚያስችለውን ተቋማዊ ለውጥ እያካሄደ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

አገልግሎት አሰጣጡን ከጊዜ ወደ ጊዜ በማሻሻል ዜጎችን ተጠቃሚ እያደረገ ሲሆን፥የዲጂታል አገልግሎት መጀመሩም ትልቅ ለውጥ የሚያመጣ ነው ብለዋል።

ሚኒስቴሩ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመቀናጀት የቴሌሳይን (teleSign) እና ዲጂታል ሞፋ (Digital MoFA) የተሰኙ ቴክኖሎጂ መር አገልግሎቶችን በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል።

የዲጂታል ሥርዓቶቹ ከየትኛውም ቦታ ሆነው እንዲህ አይነት ዘመናዊ አገልግሎት ለማግኘት ሲናፍቁ ለነበሩ የዲያስፖራ አካላትና መላው ዜጎች ትልቅ የምስራች መሆናቸውን ጠቅሰዋል።

በተጨማሪ ህጋዊ ተቀባይነት ያለውና የሰነዶችን ኦሪጅናልነት የሚያረጋግጥ የዲጂታል ፊርማ ስርዓትን ስራ ላይ ማዋል ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል።

የላቁ የኢንክሪፕሽን ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ሰነዶች እንዳይለወጡና እንዳይጭበረበሩ ብሄራዊ ዋስትና መስጠት እንዲሁ።

አገልግሎቱን ከብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) ጋር በማስተሳሰር፣ የተገልጋይ ማንነት ማረጋገጫ ስርዓት መዘርጋቱንም ጠቅሰዋል።

ዲጂታል አገልግሎቱ በውጭ ጉዳይ፣በሰነዶች ማረጋገጫ እና በፍትህ ሚኒስቴር መካከል የተቀናጀ የመረጃ ፍሰት እንደሚፈጥርም አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም