የኢትዮጵያ አየር መንገድ በምዕራብ አፍሪካ የአውሮፕላን ጥገና ማዕከል ለመገንባት የተግባር ምዕራፍ ላይ ደርሷል - ኢዜአ አማርኛ
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በምዕራብ አፍሪካ የአውሮፕላን ጥገና ማዕከል ለመገንባት የተግባር ምዕራፍ ላይ ደርሷል
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በምዕራብ አፍሪካ የአውሮፕላን ጥገና ማዕከል ለመገንባት የአዋጭነት ጥናቱን አጠናቆ የተግባር ምዕራፍ ላይ መድረሱን የአየር መንገዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ፡፡
በአዲስ አበባ ለሶስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የአፍሪካ የጥገና፣ ዕድሳትና ኦፕሬሽን ኮንፍረንስ 2026 ዛሬ ተጠናቋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው በኮንፍረሱና በሌሎች የአየር መንገዱ ወቅታዊ አንቅስቃሴዎች ዙሪያ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
ዋና ሥራ አስፈፃሚው በማብራሪያቸው፤ የተሟላ የጥገና፣ እድሳትና ኦፕሬሽን አገልግሎት ስኬታማ አየር መንገድ መገንባት ያስችላል ብለዋል።
በአፍሪካ የጥገና፣ ዕድሳትና ኦፕሬሽን አገልግሎት ክፍተት ያለበት በመሆኑ የአየር መንገዶችም ደካማ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በአፍሪካ ጠንካራ የጥገና፣ ዕድሳትና ኦፕሬሽን አገልግሎት ለመስጠት ሰፊ ሀብትና ዕውቀት ይፈልጋል ያሉት አቶ መስፍን፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የአፍሪካ አየር መንገዶች በትብብር መስራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል።
አፍሪካ ዕምቅ አቅም ያላቸው ወጣቶች እንዳሏት ገልጸው፤ ወጣቶችን አሰልጥኖ ማሰማራት ይገባል ብለዋል።
በተለያዩ ዓለማት ካሉ የአየር መንገድ የጥገና፣ ዕድሳትና ኦፕሬሽን ተቋማት ጋር በጋራ መስራት እንደሚገባም ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ አየር መንገድ የጥገና፣ ዕድሳትና ኦፕሬሽን አገልግሎት ለብዙ ዓመታት ሰርቻለሁ ያሉት አቶ መስፍን፤ የአውሮፕላን ጥገና ክፍል ለኢትዮጵያ አየር መንገድ የስኬት ቁልፍ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የስኬት ምስጢር በአየር መንገዱ ያለው የተሟላ የጥገና፣ ዕድሳትና ኦፕሬሽን አገልግሎት መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአውሮፕላን ጥገና ክፍል ለአፍሪካና ለሌሎች ዓለም ሀገራት አውሮፕላኖች ጭምር የጥገና አገልግሎት እንደሚሰጥ ገልጸው፤ ኮንፍረንሱ የአየር መንገዱን አቅም ለአፍሪካውያን ያሳየንበት መድረክ ነው ብለዋል፡፡
ከዚህም ባለፈ አስካይ ከተባለ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አጋር ጋር በመተባበር ምዕራብ አፍሪካ ላይ የጥገና ማዕከል ለመክፈት የአዋጭነት ጥናቱን አጠናቆ ወደ ተግባር ለመግባት በዝግጅት ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በመካከለኛው ምሥራቅ አካባቢ በተከሰተው ጦርነት ምክንያት በረራ ያቋረጠባቸው ከተሞች እንደነበሩ አስታውሰው፤ የቀጣናው ሀገራት አየር መንገዶች በረራ በመጀመራቸውና አየር መንገዱ የራሱን የድህንነት ግምገማ በማድረግ በአምስት ከተሞች በረራ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡
የቀጣናውን የጸጥታ ሁኔታ በቅርበት እየተከታተሉ መሆኑን ገልጸው፤ ሁኔታውን እያየን ወደ ነበርንበት መደበኛ የበረራ ሥራችን እንመለሳለን ነው ያሉት፡፡
በአፍሪካና ሌሎች ዓለማት መካከል ያለውን መንገደኛ ጨምሮ ብዙ መንገደኞችን እናጓጉዝ ነበር ያሉት አቶ መስፍን፤ የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት የኢትዮጵያ አየር መንገድን ጨምሮ ሌሎች አማራጮችን እንዲያዩ አድርጓቸዋል ብለዋል፡፡