ቀጥታ፡

የማዕከል ወደ ሥራ መግባት በክልሉ የሚገኘውን ሰፊ የእንስሳት ሀብት ወደ ላቀ የኢኮኖሚ ጥቅም ለመለወጥ ያስችላል

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የአፋር ሰመራ ሁለተኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል ወደ ሥራ መግባቱ በክልሉ የሚገኘውን ሰፊ የእንስሳት ሀብት ወደ ላቀ የኢኮኖሚ ጥቅም ለመለወጥ ያስችላል ሲሉ የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መስተዳደር አወል አርባ ገለጹ።

የአፋር ሰመራ ሁለተኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል ወደ ሥራ መግባቱ የአርብቶ አደሩንና የነጋዴውን ተጠቃሚነት በማሳደግ ረገድ ትልቅ ሚና ያለው መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሣሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገልጸዋል።

በአፋር ክልል የተገነባው የሰመራ ሁለተኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል በዛሬው ዕለት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል።   

ማዕከሉን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሣሁን ጎፌ (ዶ/ር) እና የአፋር ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አቶ አወል አርባ በጋራ ምረቃውን በማከናወን ስራ አስጀምረዋል።  

በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሣሁን ጎፌ (ዶ/ር)፣ መንግሥት የቀየሰው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም በንግዱ ዘርፍ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል።  

በተቀረጸው የንግድ ሪፎርም መሠረትም በርካታ የገበያ መሠረተ ልማቶች እየተገነቡ ይገኛሉ ብለዋል።    

በአሁኑ ወቅት በተለያዩ አካባቢዎች ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ 10 የሁለተኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከላት ግንባታ ላይ ይገኛሉ ብለዋል።   

ዛሬ የተመረቀው የሰመራ ማዕከልም ከ70 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት መሆኑን ገልጸዋል።    

ኢትዮጵያ ከሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ወዲህ ከቁም እንስሳት ዘርፍ የምታገኘው ገቢ እያደገ መምጣቱን ጠቁመዋል።  

በ2017 በጀት ዓመት ከዘርፉ 60 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን አስታውሰው፤ በያዝነው በጀት ዓመት ስምንት ወራት ብቻ 39 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን አስታውቀዋል።   

የአፋር ክልል የእንስሳት ሀብት ለሀገሪቷ የውጭ ምንዛሬ ግኝት ትልቅ አቅም ያለው መሆኑን ገልጸው፤ የማዕከሉ መገንባት የለውጡ መንግሥት ለአርብቶ አደሩ ያለውን ውግንና በተግባር ያረጋገጠበት ነው ብለዋል።  

ማዕከሉ ወደ ሥራ መግባቱ የአርብቶ አደሩንና የነጋዴውን ተጠቃሚነት በማሳደግ ረገድ ትልቅ ሚና ያለው መሆኑንም ጠቁመዋል።

የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ርዕሰ መሥተዳደር አወል አርባ በበኩላቸው፤ የማዕከሉ ወደ ስራ መግባት በክልሉ የሚገኘውን ሰፊ የእንስሳት ሀብት ወደ ላቀ የኢኮኖሚ ጥቅም ለመለወጥ ያስችላል ብለዋል።

ማዕከሉ በተያዘለት የጊዜ ተጠናቆ ለአገልግሎት መብቃቱን ጠቁመው፤ ይህም መንግሥት ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረትና የኢኮኖሚ አካታችነት ማሳያ መሆኑን አብራርተዋል። 

ማዕከሉ ለሚሌ (Quarantine) የእንስሳት ማቆያ ቅርበት ያለው በመሆኑ፣ የእንስሳት ወጪ ንግድን ለማሳለጥና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ ትልቅ አበርክቶ ይኖረዋል ብለዋል። 

አርብቶ አደሩ የእንስሳት ሃብቱን በቀጥታ ለገበያ እንዲያቀርብ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠሩም በላይ፣ በዘርፉ ለተሰማሩ ነጋዴዎች ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል ብለዋል። 

ማዕከሉ ለእንስሳት ግብይት የሚያስፈልጉ ሁሉንም ዓይነት መሠረተ ልማቶችን አሟልቶ የተገነባ በመሆኑ ግብይቱ ቀልጣፋና ሥርዓት ያለው እንዲሆን ያስችላል ነው ያሉት።

የዚህ ማዕከል መከፈቱ የቁም እንስሳት ንግድ ዳግም እንዲያንሰራራ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። 

የእንስሳት ግብይት እንዲሳለጥና ውጤታማ እንዲሆን ከክልሉ መንግሥት የሚጠበቅብንን ሁሉ እናደርጋለን ሲሉም አረጋግጠዋል።

ይህ የግብይት ማዕከል ወደ ሥራ መግባቱ በክልሉ የሚገኘውን ሰፊ የእንስሳት ሀብት ወደ ተሻለ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለመለወጥ የሚደረገውን ጥረት በእጅጉ ያግዛል ተብሎ ይጠበቃል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም