ቀጥታ፡

የከተሞችን እድገትና የነዋሪዎችን ኑሮ ለማሻሻል ትኩረት ተሰጥቷል

ጅግጅጋ፣መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፡- መንግሥት የከተሞችን እድገትና የነዋሪዎችን ኑሮ ለማሻሻል ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑ ተመለከተ።

የኢትዮጵያ ከተሞች የትብብር መድረክ በሶማሌ ክልል ለሚገኙ አባል ከተማ ከንቲባዎችና ለክልል የዘርፉ ኃላፊዎች በከተማ አመራር፣ ባልተማከለ አስተዳደርና አገልግሎት አሰጣጥ እንዲሁም በገቢ ማሳደግ ዙሪያ በጅግጅጋ ከተማ አውደጥናት እያካሄደ ነው።


 

የኢትዮጵያ ከተሞች ትብብር መድረክ ዋና ዳይሬክተር አቶ አንዱዓለም ጤናው በወቅቱ እንደገለጹት  የትብብር መድረኩ የተለያዩ ስትራቴጂካዊ ስልቶች በማዘጋጀትና ከተሞች የሚሰጡትን  አገልግሎት በብቃት መከወን እንዲችሉ የተለያዩ ድጋፎች የሚያደርግ ነው።

የከተሞች ትብብር መድረኩ  ከተሜነትን ለማስፋፋትና የነዋሪዎቹን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል ታስቦ በከተማ አስተዳደሮች በጎ ፍቃድ የተመሠረተ መሆኑን አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ከተሞች የትብብር መድረክ በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ የሚገኙ 178 ከተሞችን በአባልነት የያዘ  መሆኑን ገልጸዋል።


 

መደረኩ የከተሞች የማማሪያ፣ የእውቀት ሽግግርና የልምድ ልውውጥ ማድረጊያ መሆኑን ጠቁመዋል።

ትብብር መድረኩ ከተሞች የሚሰጡት አገልግሎት ጥራት ያለው እንዲሆን የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ይገኛል ሲሉም አክለዋል ።

አውደጥናቱ ከተሞች የማዘጋጃ ቤት ገቢን በማሻሻል፣ በማዘመንና የሀብት ማሰባሰብ ሥራዎችን የሚያጎለብቱበትን  ተግባር የሚያዳብር መሆኑን ተናግረዋል።

እንዲሁም መሰረታዊ አገልግሎቶችን በጥራትና በፍጥነት ለመስጠት የሚያስችሉና እድገታቸውን የሚያፋጥኑ ሥራዎችን  የሚደግፍ መሆኑን ጠቁመው ከተሞች እንዲያደጉና እንዲስፋፉ የሚደረጉ ጥረቶችን የሚደግፍ  መሆኑንም አመልክተዋል።


 

የሶማሌ ክልል ከተማና ኮንስትራክሽን ቢሮ ሃላፊ አቶ አህመድ ሹክሪ በበኩላቸው  በሶማሌ ክልል 32 ከተሞች የኢትዮጵያ የከተሞች ትብብር መድረክ አባል ናቸው ብለዋል።

በከተሞች ማዘጋጃ ቤቶች ቀልጣፋና ጥራት ያለዉ አገልግሎት መስጠት የሚያስችላቸውን ሥራዎች እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።

 አውደጥናቱ የከተሞችን ሥራ የማከናወን አቅም የሚያዳብር መሆኑን ጠቅሰው ከተሞቹ አገልግሎቶችን በጥራትና በፍጥነት ለመስጠት የሚያስችላቸው መሆኑን ተናግረዋል።

ማዘጋጀት ቤቶች በዘመናዊ መልኩ  አገልግሎቶችን በዲጂታል ለመስጠት የሚያስችላቸውን ተግባራት ማከናወን  እንዲችሉ አቅም የሚያዳብር ነው ሲሉም አክለዋል።

በመድረኩ በቅርቡ ትብብር መድረኩን ለተቀላቀሉ ከተሞች ዕውቅና እንደሚሰጥ ተመላክቷል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም