ቀጥታ፡

የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ሥርዓት የማዕድን ሃብት የዕድገት ምሰሶ የሚሆንበትን ወሳኝ ዕድል ፈጥሯል

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ሥርዓት የማዕድን ሃብት የዕድገት ምሰሶ የሚሆንበትን ወሳኝ ዕድል መፍጠሩን የዘርፉ ምሁራን ገለጹ።

የዘርፉ ምሁራን ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ የማዕድን ሃብት ልማት የዘርፉን ምርታማነት በማነቃቃት ብዝኅ የተፈጥሮ ጸጋን ወደ ጥቅም መለወጥ እያስቻለ ስኬት እያስገኘ ነው።

በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የጂኦሎጂና ማዕድን ምህንድስና ትምህርት ክፍል መምህር ግርማ ወልደትንሳኤ(ዶ/ር)፤ ሀገራዊ ለውጡ ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሃብቷን የምትጠቀምበት ዕድል ፈጥሯል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ሥርዓትም የማዕድን ሃብት ልማት የአሰራር ውስንነቶችን በመቅረፍ አስቻይ የተፈጥሮ ሃብት ንግድና ኢንቨስትመንት የምርታማነት ምኅዳር መፍጠሩን ገልጸዋል።

የተፈጥሮ ጸጋዎች በሀገር ዕድገት ገንቢ ሚና የሚወጡበት አስቻይ ሁኔታ መፈጠሩም የማዕድን ሃብቶችን በመለየት ተገቢውን የአስተዳደር ሥርዓት መፍጠር እንዳስቻለ ተናግረዋል።

የማዕድን ሀብት ለሀገር ዕድገት የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ ለማሳደግ የዘርፉን ንግድና ኢንቨስትመንት ውጤታማነት የሚያስጠብቅ የጥናትና ምርምር ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም መክረዋል።

በተለይም የማዕድን ጸጋዎችን የዕሴት ሰንሰለት ለማሻሻል በሚደረገው ጥረት የአካባቢ ደኅንነትና ዘላቂነትን በማስጠበቅ የዘርፉ ተዋናዮች በቅንጅት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።


 

በማዕድን ዘርፍ ኢንቨስትመንት የአርዲኮ የግል ካምፓኒ ሥራ አስኪያጅ ወዳጄ አበበ(ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሽግግር ውስጥ የማዕድን ዘርፍ የድርሻውን የሚያበረክትበት ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ሥርዓትና የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያም ለማዕድን የኢንቨስትመንት ምርታማነት ወሳኝ ዕድል መፍጠራቸውን ገልጸዋል።

ለዚህም ውጤታማ የጥናትና ምርምር ሥራዎችን በማፍለቅ በተፈጥሮ ጸጋዎች የተፈጠረውን የምርታማነት መነቃቃት የበለጠ ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።

በቀጣይም የማዕድን ሃብት ምርታማነትን ለማስቀጠል በዘርፉ የተካነ የሰው ሃይልና ቴክኖሎጂ ማፍለቅ እንደሚገባ ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም