ቀጥታ፡

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የተቀላጠፈ አገልግሎት እየሰጠን ነው

ባህርዳር፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፡-መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ከዚህ ቀደም የነበረን መጉላላት በማስቀረት በተቀላጠፈ ሁኔታ እንድንገለገል አስችሎናል ሲሉ የባህር ዳር ማዕከል ተገልጋዮች ገለፁ።

ማዕከሉ በሚሰጠው አገልግሎት የደንበኞችን የእርካታ መጠን በእጅጉ ማሳደግ መቻሉም ተመልክቷል።

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በተለያዩ ተቋማት የሚሰጡ አገልግሎቶችን በአንድ ማዕከል በተደራጀ አግባብ ለመስጠት የሚያስችል አሰራር ነው።

በዚህም በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር በመዘርጋት ደንበኞች ይደርስባቸው የነበረውን እንግልትና ድካም በእጅጉ ያስቀረ አገልግሎትን ተደራሽ ማድረግ ተችሏል።


 

በባህር ዳር በሚገኘው የክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሲገለገሉ ያገኘናቸው አቶ አወል ሞሳ ለኢዜአ እንደገለፁት በማዕከሉ እየተሰጠ ያለው አገልግሎት እንግልትን ያስቀረ ነው።

በተለይም ከዚህ ቀደም በቀበሌና በክፍለ ከተማ  አገልግሎት ለማግኘት እጅግ አስቸጋሪ እንደነበር ጠቅሰው፤ አሁን ላይ በማዕከሉ የተቀላጠፈ መስተንግዶ እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል።

በማዕከሉ ከ10 ደቂቃ ባልበለጠ ጊዜ መስተናገድ እንደቻሉ አንስተው፤ ይህም ቀደም ሲል በአራትና በአምስት ቀናት የማይሳካ እንደነበር አስታውሰዋል።

አገልግሎት አሰጣጡ ጊዜንና ጉልበትን ከብክነት ያስቀረ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከመሬትና ከካርታ አሰጣጥ ጋር የተያያዙ አገልግሎቶችም በአፋጣኝ ወደ ማዕከሉ ሊገቡ እንደሚገባም ተናግረዋል።


 

ከዚህ ቀደም ማንኛውንም አገልግሎት ከቀበሌም ሆነ ከክፍለ ከተማ ለማግኘት እጅግ አድካሚ እና አስቸጋሪ እንደነበር የገለፀው ሌላው ተገልጋይ አለማየሁ ሙሉጌታ የአገልግሎት አሰጣጡ ልምድና ተሞክሮ ወደ ታች ሊወርድ እንደሚገባ ተናግሯል።

አሁን ላይ በማዕከሉ የንግድ ፈቃድ ለመዝጋት መጥቶ በአጠረ ጊዜ ያለምንም ድካምና እንግልት መጨረስ እንደቻለም አስረድቷል።

በባህር ዳር በሚገኘው የክልሉ የመሶብ የአንድ ማዕከል አስተባባሪ አቶ ተማረ አቤ በበኩላቸው፤ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የህዝብን እንግልት በቀልጣፋ አገልግሎት ለመፍታት የተዘረጋ አሰራር ነው ብለዋል።

በማዕከሉ የህዝብ አገልግሎት የሚበዛባቸውና የከፋ እንግልት ይስተዋልባቸው የነበሩ ተቋማትን በፍጥነት በመለየት ወደ ማዕከሉ እንዲገቡ የማድረግ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል።


 

እስካሁን በተደረገ ጥረትም 15 የክልልና የፌደራል ተቋማትን ወደ ማዕከሉ በማስገባት 61 አገልግሎቶች ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ እንደተቻለም ተናግረዋል።

ባለፉት ጊዜያት በተደረገ ጥረትም ከ36 ሺህ በላይ ተገልጋዮችን ማስተናገድ የተቻለ ሲሆን በቴክኖሎጂ ታግዞ በተደረገ ጥናትም የአገልግሎት አሰጣጥ የእርካታ መጠንን 97 በመቶ ማድረስ ተችሏል ብለዋል።

የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት በከተማ ደረጃ በባህር ዳርና ደሴ ከተሞች እየተሰጠ ሲሆን በቅርቡም ጎንደርን ጨምሮ በሌሎች ስድስት ከተሞች አገልግሎቱን ለማስፋት እየተሰራ ይገኛል።

ከዚህም ባለፈ በ25 መካከለኛና አነስተኛ ከተሞች አገልግሎቱን ለማስፋት ስልጠና ከመስጠት ባለፈ ሌሎች ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆናቸውንም አብራርተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም