ሚኒስቴሩ በጋሞ ዞን ያስገነባውን የጸሀይ ኃይል ማመንጫ ለአገልግሎት አበቃ - ኢዜአ አማርኛ
ሚኒስቴሩ በጋሞ ዞን ያስገነባውን የጸሀይ ኃይል ማመንጫ ለአገልግሎት አበቃ
አርባ ምንጭ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በጋሞ ዞን ጋርዳ ማርታ ወረዳ በ500 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባው የጸሀይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ለአገልግሎት አበቃ።
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታው ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ(ዶ/ር) በምረቃው ላይ እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቱ 710 ኪሎ ዋት ኃይል ማመንጨት የሚችል ሲሆን፣ 6 ሺህ 500 አባወራዎችን ተጠቃሚ ያደርጋል።
ፕሮጀክቱ የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እንደሚያሳልጥ ጠቅሰው፤ በተለይ ለወጣቶች የሥራ ዕድል ከመፍጠር አኳያ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል።
ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን የተናገሩት ሚኒስትር ዴኤታው፣ የአካባቢው ማህበረሰብ ለተገነባው መሠረተ ልማት ተገቢውን ጥበቃ እንዲያደርግም አሳስበዋል።
ለአካባቢው ማህበረሰብ የኃይል ስርጭቱን ለማዳረስ 7 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን መካከለኛ መስመር እንዲሁም 17 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ዝቅተኛ መስመር ተዘርግቷል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በውሃ፣ በፀሐይ ብርሃን፣ በነፋስና በሌሎች የታዳሽ ኃይል ምንጮች ወደ 150 ጊጋ ዋት ማመንጨት የሚያስችል አቅም ያላት ቢሆንም፤ እስካሁን ጥቅም ላይ የዋለው 9 ነጥብ 5 ጊጋ ዋት ብቻ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል።
የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ደምስ አድማሱ (ዶ/ር)፤ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በጋርዳ ማርታ ወረዳ ህዝብን ተጠቃሚ ያደረገ ፕሮጀክት ገንብቶ በማስረከቡ ምስጋና አቅርበዋል።
አካባቢው ከመሠረተ ልማት ርቆ በመቆየቱ ህዝቡ የኃይል ተጠቃሚ ሳይሆን መቆየቱን አስታውሰው፤ ፕሮጀክቱ መንግስት የገባውን ቃል በተግባር ያሳየበት ነው ብለዋል።
በተለይ የጤና ተቋማት የላቦራቶሪ አገልግሎት እንዲሰጡ እንዲሁም የትምህርት ተቋማት ቴክኖሎጂን እንዲጠቀሙ በማስቻል ረገድ ፕሮጀክቱ ጉልህ ፋይዳ እንዳለውም ተናግረዋል።