ቀጥታ፡

በዞኑ ያለውን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም ከዝናብ ጠባቂነት ለመላቀቅ በተሠራው ሥራ ውጤት ተገኝቷል

ጅማ፤ መጋቢት 21/2018(ኢዜአ)፡-በጅማ ዞን ያለውን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም ከዝናብ ጠባቂነት በመላቀቅ በዓመት ሁለት ጊዜ ለማምረት በተሠራው ሥራ አበረታች ውጤት እየተገኘ ነው።

በዞኑ ከ930 በላይ የውኃ ምንጮች ያሉ ሲሆን፣ ይህን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም አርሶ አደሩ በመስኖ የተሻለ ምርት እንዲያመርት ሲሠራ ቆይቷል።

የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም እንዳሉት፤ በዘንድሮ ዓመት 63 ሺህ 180 ሄክታር መሬት በአትክልት ምርት ተሸፍኗል። 


 

ከዚህም 10 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል የአትክልት ምርት ተሰብስቧል ነው ያሉት።

ከዚህ ቀደም በቂ የገበያ ትስስር ባለመፈጠሩ አርሶ አደሩ ምርቱን ለገበያ ለማቅረብ ሲቸገር መቆየቱን የተናገሩት ኃላፊው፤ አሁን ላይ ይህ ችግር ተቀርፎ ነጋዴው ያለማንም ጣልቃ ገብነት በቀጥታ ወደ ስፍራው ሄዶ ከአርሶ አደሩ እንዲረከብ እየተደረገ ነው ብለዋል።

በሂደቱ አርሶ አደሮች ተደራድረው የራሳቸውን የዋጋ ተመን በማውጣት ምርታቸውን በስምምነት እንዲያቀርቡ መንገድ መክፈቱን ገልጸዋል። 

ከዚህ በተጨማሪም ሴት አርሶ አደሮችን በማደራጀት አምርተው ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።

በጅማ ዞን ሰኮሩ ወረዳ ኡንኩሬ ቀበሌ ነዋሪ የሆነችው ሰብለ አየለ፤ በሽንኩርት፣ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመን እና በሌሎችም የአትክልት ምርቶች ተሰማርታ ውጤታማ መሆኗን ትናገራለች።

የስራውን  ውጤታማነት በመረዳት ስድስት ሴቶችን ጨምራ በማደራጀት በዚህ ዓመት ከ350 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘቷን ገልፃ በቀጣይም እየተሰበሰበ ካለው የሽንኩርት ምርት የ300 ሺህ ብር ገቢ ለማግኘት ማቀዷን ነው የገለጸችው። 

በአካባቢው ያለውን ውኃ በመጠቀም ወደፊት በስፋት አምርታ ለበርካቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ማቀዷንም አክላለች።

ሌላኛው የጅማ ዞን ቀርሳ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ነጂብ አባ ራያ የውሀ ፓምፕ በመጠቀም አምርተው ለገበያ በማቅረብ ከ 300 ሺህ ብር በላይ ገቢ አግኝተዋል።

በቀጣይም የተሻለ ምርት በማምረት ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እየሰሩ ሲሆን አሁን ላይም ተጨማሪ የሽንኩርት ምርት ለገበያ እያቀረብኩ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም