በምዕራብ ሸዋ ዞን በሚቀጥለው ክረምት የሚተከል የቡና ችግኝ ተዘጋጀ - ኢዜአ አማርኛ
በምዕራብ ሸዋ ዞን በሚቀጥለው ክረምት የሚተከል የቡና ችግኝ ተዘጋጀ
አምቦ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በ220 የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች በሚቀጥለው ክረምት የሚተከል የቡና ችግኝ መዘጋጀቱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ።
የጽሕፈት ቤቱ የቡና፣ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ቡድን መሪ አቶ ቶሎሳ አራርሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ አርሶ አደሩን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በቡናና ፍራፍሬ ልማት በማሳተፍ ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ እየተሠራ ይገኛል።
ለዚህም በመጪው ክረምት 5 ነጥብ 7 ሚሊዮን የቡና ችግኝ ለማዘጋጀት ታቅዶ፣ እስካሁን 5 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞች ተዘጋጅተዋል።
እንደ ቡድን መሪው ገለጻ፤ ችግኞቹ ከጅማ ግብርና ምርምር ማዕከል የተገኙ የተሻሻሉ ዝርያዎች ሲሆኑ፣ በሽታን የመቋቋም አቅም ያላቸውና በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ምርት መስጠት የሚጀምሩ ናቸው።
የችግኝ ዝግጅቱ በ220 የመንግሥትና የግል የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተከናወነ ሲሆን፣ በሥራው ላይ 16 ሺህ 415 አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ገልጸዋል።
የተዘጋጀው የቡና ችግኝ ሲተከል አንድ ሺህ ሄክታር ገደማ አዲስ መሬት በቡና መሸፈን እንደሚያስችልም ጠቅሰዋል።
ከአዲስ ተከላው በተጓዳኝ ያረጁና ከምርት ውጭ የሆኑ የቡና ዛፎችን የማደስ ሥራም እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።