የአመራር አባላት ኢንተርፕርነርሽፕ ክህሎት መጎልበት ለፈጠራና ለለውጥ መሠረት ነው- ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ - ኢዜአ አማርኛ
የአመራር አባላት ኢንተርፕርነርሽፕ ክህሎት መጎልበት ለፈጠራና ለለውጥ መሠረት ነው- ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ
አዲስ አበባ፤መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦የአመራር አባላቱ ኢንተርፕርነርሽፕ ክህሎት መጎልበት ለፈጠራና ለለውጥ መሠረት ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ ገለጹ።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት "አመራርና የመጪው ዘመን ዝግጁነት "በሚል መሪ ሀሳብ የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና መስጠት ጀምሯል።
ሥልጠናው የአመራር አባላት ሥራቸውን በአንተርፕረነርሽፕ አስተሳሰብ እንዲመሩና ለተለዋዋጭ የሥራ አካባቢዎች ዝግጁ እንዲሆኑ ታስቦ የተዘጋጀ እንደሆነ ተመላክቷል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ በዚሁ ወቅት ሥልጠናው የምክር ቤት አባላት ካላችሁ የላቀ የሕዝብ አመራር ልምድ በመነሳት ሀገራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎችን በላቀ ብስለትና በሥራ ፈጠራነት መንፈስ እንድትቀርጹ ለማገዝ ነው ብለዋል።
አባላቱ ያላቸው ዕውቀትና ልምድ ውጤታማ እና ፍሬያማ የሆኑ ሥራዎች ለመስራት የሚያግዝ እንደሆነ ጠቁመዋል።
ይህም ችግሮችን በፈጠራ፣ በፍጥነት እንዲሁም በባለቤትነት መንፈስ ለመፍታትና አዳዲስ የአገልግሎት ዘርፎችን ለመፍጠር የሚያስችል ነው ብለዋል።
የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በበኩላቸው፤ የዘመኑን ፈጣን ለውጥ ለመቋቋም የአመራሩ የሥራ መርህ መዘመን እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል።
የአመራር አባላት እንደ አንድ ሥራ ፈጣሪ የችግሮችን መፍትሔ በአዲስ የፈጠራ መንገድ የመቅረጽ፣አዳዲስ ዕድሎችን የመለየት እና በሥራ ሂደት ውስጥ የመፍጠንና የመፍጠር ብቃት ሊኖራቸው እንደሚገባም ገልጸዋል።
በመሆኑም ይህ ሥልጠና በምክር ቤቱ አባላት ዘንድ የስትራቴጂክ አመራር ክህሎትን ከማሳደጉ ባሻገር ሀገራዊ የልማት ግቦችን በብቃት ለማሳካት የሚረዳ የተቀናጀ የአሠራር ሥርዓት ለመገንባት ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል።
በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፣ የምክር ቤቱ አባላትና የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።